አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 18፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የሶማሊያው ፕሬዚዳንት ሞሀመድ ፋርማጆ ጠቅላይ ሚኒስትር ሞሀመድ ሁሴን ሮብሌ የህዝብ መሬት ለግል ጥቅም አውለዋል በሚል ክሥ እና በምርጫ ወቅት ባሳዩት ደካማ አፈጻጸም ከሥራ አግደዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ የተቀሩት ካቢኔዎቻቸው የተለመደ ሥራቸውን እንዲቀጥሉም ነው ያዘዙት፡፡
ፕሬዚዳንት ፋርማጆ በቤተ መንግሥታቸው በሰጡት መግለጫ፥ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ መታገድ የሶማሊያ መከላከያ ንብረት የሆነውን በሞቃዲሾ ሊዶ ባህር ዳርቻ አካባቢ የሚገኝ መሬት ለግል ጥቅማቸው በማዋላቸው እና ከዚሁ ጋር ተያይዞ በሙስና በመወንጀላቸው እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡
ፋርማጆ፥ የሀገራቸው ፕሬዚዳንታዊ መመሪያ የመንግስት ባለሥልጣናት የህዝብን ንብረት ለግል ጥቅም እንዳያውሉ እንደሚከለክል ጠቅሰው፥ ማንኛውም የመንግስት ባለሥልጣን ከእንደዚህ ዓይነት ድርጊት እንዲቆጠብም ማሳሰባቸውን ኔሽን ዘግቧል፡፡