አዲስ አበባ፣ ጥር 8፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቦረና ዞን በድርቅ ምክንያት ችግር የደረሰባቸውን ወገኖች ለመደገፍ 50 ሚሊየን ብር የሚገመት ድጋፍ አድርጓል፡፡
ከተማ አስተዳደሩ በድርቅ ምክንያት ሊደርስ የሚችለውን ጉዳት ለመቀነስ የእንስሳት መኖ ፣ የውሃ ቦቴዎች፣ ሮቶዎች፣ የህክምና መድሃኒት እና በድርቁ ለተጎዱ ወገኖች ቀለብ የሚሆን የ50 ሚሊየን ብር ድጋፍ አስረክቧል፡፡
ድጋፉን ያስረከቡት በምክትል ከንቲባ ማእረግ የፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ ወ/ሮ ነጂባ አክመል፥ ድጋፉ የከተማ አስተዳደራችንና የከተማችን ነዋሪዎች በዚህ ችግር ወቅት ከጎናችሁ መሆናችን፣ ለናንተ ያለንን ፍቅር ለመግለፅ እና በቀጣይም ችግሩ በዘላቂነት እስኪፈታ ድረስ በዞኑ ላለው ከፍተኛ የእንስሳት ምርት የገበያ ትስስር ከመፍጠር ጀምሮ ከጎናችሁ መሆናችንን ለማረጋገጥ ነው ብለዋል፡፡
እንዲሁም የቦረና ዞን አስተዳዳሪ አቶ ጃርሶ ቦሩ እደተናገሩት÷ አዲስ አበባ የሁላችም መጠለያ ናት ያሉ ሲሆን የከተማ አስተዳደሩም ድርቅ ካጋጠመ ጊዜ ጀምሮ ላደረገው ድጋፍ በዞኑ ህዝብ ስም ምስጋና አቅርበዋል፡፡
ከተማ አስተዳደሩ የክረምት እና የበልግ ዝናብ ወቅቱን ጠብቆ ባለመጣሉ ምክንያት ቦረና ዞን በተከሰተው ድርቅ ምክንያት እየደረሰ ያለው ጉዳት ከተሰማበት ጊዜ ጀምሮ የተለያዩ ድጋፎችን ሲያደርግ ቆይቷል፡፡
በዚህም ከዚህ ቀደም በመጀመሪያ ዙር የከተማውን ህብረተሰብ በማስተባበር ከ51 ሚሊየን ብር በላይ የአይነት ድጋፍ በማስባሰብ ለዞኑ ማስረከቡ ይታወሳል፡፡