የሀገር ውስጥ ዜና

በኮምቦልቻ ኢንዱስትሪ ፓርክ የሚገኙ 3 ኩባንያዎች ምርታቸውን ወደ ውጭ መላክ ጀመሩ

By Alemayehu Geremew

February 03, 2022

አዲስ አበባ፣ ጥር 26፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በህወሓት የሽብር ቡድን ጉዳት ደርሶባቸው ከነበሩትና በኮምቦልቻ ኢንዱስትሪ ፓርክ ሥር የሚገኙት ሦስት ኩባንያዎች ምርታቸውን ወደ ውጭ ገበያ ማቅረብ ጀመሩ፡፡

በፓርኩ ከሚገኙት አራት ኩባንያዎች ሦስቱ ስራ መጀመራቸው የተገለጸ ሲሆን÷ ምርታቸውን ለውጭ ገበያ ማቅረብ መጀመራቸውም ተገልጿል።

አዲዳስ እና ፑማ ለመሳሰሉ አለም አቀፍ ተቋማት ምርቶቹ የሚያቀርቡ መሆኑን ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት የገለጹት የኩባንያው ስራ አስኪያጅ ዎልተር ፎድሊ÷ ከ5 ሚሊየን ዶላር በላይ ውድመት ቢደርስብንም በቶሎ ወደ ስራ ገብተናል ብለዋል።

በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን የኮምቦልቻ ኢንዱስትሪ ፓርክ ስራ አስኪያጁ አቶ ሙሉጌታ መኮንን በበኩላቸው የቀረው አንድ ኩባንያ በቅርቡ ስራ እንደሚጀምር ገልጸው ÷ 24 ሰዓት በማምረት ለውጭ ገበያ ምርቶች እየቀረቡ መሆኑንም ተናረዋል።

በፓርኩ ውስጥ ከሦስት ሺህ በላይ ዜጎች የስራ እድል እንደተፈጠረላቸው የተገለጸ ሲሆን÷ በሦስቱ ተቋማት ውስጥ የሚሠሩ ከ90 በመቶ በላይ ሰራተኞች ወደ ስራ መመለሳቸውም ተመላክቷል።

በጣሊያን፣ በአሜሪካ፣ በቻይና ፣ በደቡብ ኮሪያና በኢትዮጵያውያን ባለሀብቶች የተያዙት ኩባንያዎቹ÷ የውጭ ምንዛሬ በማስገኘት በኩል ሰፊ ስራ ሲሰሩ መቆየታቸውም ተገልጿል፡፡

ከሐምሌ እሰከ መስከረም ባሉት ሦስት ወራት ከ3 ነጥብ 9 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር በላይ ገቢ አስገኝተዋል ነው የተባለው፡፡

ካርቪኮ ኢትዮጵያ ተሰኘው ኩባንያ 69 በመቶ የሚሆነውን ገቢ የሸፈነ መሆኑም ተገልጿል።

በከድር መሀመድ