የሀገር ውስጥ ዜና

በጦርነቱ የተጎዱ ማህበራዊ ተቋማት የመልሶ ግንባታ ማስጀመሪያ ሥነ-ሥርዓት ተካሄደ

By Alemayehu Geremew

April 07, 2022

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 29፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በሰባት ከተሞች 18 ግንባታዎችን ለማከናወን የሚያስችል የመሠረት ድንጋይ የመጣልና ከተቋራጮች ጋር የግንባታ ውል ሥምምነት የመፈራረም ሥነ-ሥርዓት በከሚሴ ከተማ ተካሂዷል።

የደሴ ከተማ አስተዳደር የሥራ ዕድል ፈጠራና ምግብ ዋስትና ጽሕፈት ቤት ከዓለም ባንክ በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ ነው መርሃ-ግብሩን ያዘጋጁት።

18ቱ ግንባታዎች ÷ ሥምንት የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች፣ ሦስት ጤና ጣቢያዎች፣ እና ሰባት የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫዎች እንደሆኑ ተመላክቷል።

በፕሮጀክቱ በጥቅሉ 150 ሚሊየን ብር የሚያወጡ ሲሆን ÷ ሸዋ ሮቢት፣ ከሚሴ፣ ኮምቦልቻ ፣ ደሴ፣ ወልድያ፣ ላሊበላና ሰቆጣ ፕሮጀክቶች የሚከናወኑባቸው ከተሞች መሆናቸውን የአማራ ክልል የከተሞች ልማታዊ ሴፍቲኔት ከፍተኛ ባለሙያ አቶ ዘውዱ ሞኝነቴ ገልጸዋል።

እስከ ቀጣዩ ነሐሴ 2014 የሚጠናቀቁት ፕሮጀክቶች በከተሞች ልማታዊ ሴፍቲኔትና ስራ ፕሮጀክት፣ በዓለም ባንክ የገንዘብ ድጋፍና በኢትዮጵያ መንግስት ትብብር የሚሰሩ ናቸው።

ዛሬ ከፌደራልና ከክልል የስራ ሃላፊዎች፣ የሰባቱም ከተሞች ከንቲባዎች፣ ሥራ አስኪያጆችና የልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም አስተባባሪዎች በተገኙበት የመሠረት ድንጋይ የማስቀመጥ ሥነ-ሥርዓት ተከናውኗል።

በአንድነት ናሁሠናይ