አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 30፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ዓለምአቀፉ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ የትግበራ ቡድን የተሳካ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ-ግብር ማካሄዱን ገለጸ፡፡
ዳያስፖራ ቡድኑ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ-ግብሩን ያካሄደው ኢትዮጵያ ውስጥ በተከሰተው ግጭት ምክንያት የተፈናቀሉ ወገኖችን ለማቋቋም እና በተፈጥሮ አደጋዎች የተጎዱ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ለመደገፍ ነው ተብሏል፡፡
በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ስለሺ በቀለ ይህን የተቀደሰ ዓላማ ይዞ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ-ግብር ያቀናጁትን እና ገንዘባቸውን በመለገስ የተሳተፉትን የዳያስፖራ ማኅበረሰብ አባላት አመስግነዋል፡፡
አምባሳደር ስለሺ ዳያስፖራው በሁሉም ግንባር ያለውን ተሳትፎ እንዲያሳድግም ጠይቀዋል፡፡
በተለይም ስለ ኢትዮጵያ ያለውን እውነታ ለዓለምአቀፉ ማኅበረሰብ እና ፍትኅ አካላት እንዲያስረዱ መጠየቃቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል።
ዳያስፖራው ያለውን የክኅሎት እና የቴክኖሎጂ እውቀት እንዲያሻግር፣ በተቋማት ግንባታ ላይ እንዲሳተፍ እንዲሁም በዲጂታል እና በኅዝብ ዲፕሎማሲ ላይ ያላሰለሰ ተሳትፎ እንዲያደርግም ነው የጠየቁት።