የሀገር ውስጥ ዜና

“በኢትዮጵያ ኢንቨስት ያድርጉ 2023” ፎረም ነገ ይጀመራል

By Alemayehu Geremew

April 25, 2023

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 17፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) “በኢትዮጵያ ኢንቨስት ያድርጉ 2023” በሚል መሪ-ቃል የተዘጋጀ ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት መድረክ በነገው ዕለት በአዲስ አበባ ይከፈታል፡፡

መድረኩን ያዘጋጀው የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ሲሆን ፥ እስከ ሚያዝያ 20 ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ገልጿል፡፡

በመድረኩ ከዓለም ዙሪያ የተውጣጡ ባለሐብቶች ፣ የንግድ አዋቂዎች ፣ፖሊሲ አውጪዎች እና ሥራ ፈጣሪዎች ይሰባሰባሉም ነው የተባለው፡፡

አዲስ ዕይታዎች በኢትዮጵያ ያሉ የኢንቨስትመንት ዕድሎችና ባለሐብቶች መዋዕለ-ንዋያቸውን የሚያፈሱባቸው የሥራ አማራጮች እንደሚቀርቡም ኮሚሽኑ አስታውቋል፡፡

መርሐ-ግብሩ “መዋዕለ-ንዋይዎን በኢትዮጵያ ያፍሱ እና ይደጉ – ኢትዮጵያ ማራኪ የኢንቨስትመንት ዕድሎች ምድር” በሚል መሪ ቃል ይካሄዳል።

በመድረኩ ከ600 በላይ ዓለምአቀፍ ኢንቨስተሮች እንደሚሳተፉበት ተገልጿል፡፡

በሚፈጠሩት የኢንቨስትመንት አማራጮችና ዕድሎች በሚቀጥሉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ ከ3 ቢሊየን ዶላር በላይ የሚሆን መዋዕለ-ንዋያቸውን ይዘው ኢንቨስት ለማድረግ ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡ ባለሐብቶች እንደሚፈጠሩም ኮሚሽኑ በመረጃው ጠቁሟል፡፡