የሀገር ውስጥ ዜና

በኦሮሚያ ክልል ያለውን ግጭት በማስወገድ ሰላምን ለማምጣት በታንዛኒያ ሲካሄድ የቆየው የሰላም ውይይት የመጀመሪያ ምዕራፍ ተጠናቀቀ

By Alemayehu Geremew

May 03, 2023

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 25፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በኦሮሚያ ክልል ያለውን ግጭት በማስወገድ ሰላምን ለማምጣት ያለመውና በታንዛኒያ ሲካሄድ የቆየው የሰላም ውይይት የመጀመሪያ ምዕራፍ ዛሬ መጠናቀቅን መንግሥት አስታወቀ፡፡

የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ባወጣው መግለጫ÷ ውይይቱ በአብዛኛው በአዎንታዊ መልኩ የተከናወነ ቢሆንም በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ ግን በዚህኛው የውይይት ምዕራፍ ስምምነት ላይ ለመድረስ አልተቻለም ብሏል፡፡

ግጭቱን በዘላቂነትና ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለማስቆም እንዲቻል ሁለቱም አካላት የሰላም ውይይቱን መቀጠል አስፈላጊ መሆኑ ላይ ተግባብተዋል ብሏል መግለጫው።

በኢትዮጵያ ሕገ መንግሥትና እስካሁን ሲመራባቸው በነበሩ መሠረታዊ መርሖች መሠረት ግጭቱን በሰላማዊ መልኩ ለመፍታት መንግስት የጸና አቋም እንዳለውም ነው የተገለጸው፡፡

ይህንን መልካም አጋጣሚና በውይይት ችግሮችን የመፍታት በጎ ጅምር በመጠቀም÷ ጉዳዩ እልባት እንዲያገኝ የኢትዮጵያ መንግሥት ያለውን ፅኑ አቋም ዳግም ያረጋግጣል ብሏል የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት በመግለጫው፡፡

የሰላም ውይይቱን ላመቻቹና ላስተናገዱ አካላት የኢፌዴሪ መንግሥት ምስጋና አቅርቧል፡፡