የሀገር ውስጥ ዜና

የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄና ውጤቶች የፓናል ውይይት እየተካሄደ ነው

By Amele Demsew

May 07, 2023

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 29፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄና ውጤቶች የፓናል ውይይት መድረክ በሚሊኒየም አዳራሽ እየተካሄደ ነው።

በውይይቱ ላይ የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሺዴ፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ መላኩ አለበል፣ የፕላንና ልማት ሚኒስትሯ ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር )፣ የጉምሩክ ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሀላፊዎች ተገኝተዋል።

ከተጀመረ አንድ ዓመቱን ያስቆጠረው ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በማምረቻው ዘርፍ በርካታ ውጤቶችን አስገኝቷል ተብሏል፡፡

አቶ መላኩ አለበል በዚሁ ወቅት÷ የማምረቻው ዘርፍ ቀጣይነት ያለው እና ውድድር የበዛበት ዘርፍ ነው ብለዋል፡፡

በተለይም የኮሮና ቫይረስ መምጣት እና የጸጥታ ሁኔታውም ዘርፉን ይበልጥ ፈተና ላይ እንዲወድቅ እንዳደረገውም አንስተዋል ።

በዚህም የኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም እንዲወርድ እና ኢንቨስትመንት እንዲቀዛቀዝ ማድረጉንም ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የተጀመረውም ቀደም ሲል ስንከተለው ከነበረው ነባራዊ ሁኔታ በመውጣት ና ችግሩን ለመቋቋም ያለመ ነው ብለዋል ።

በተጨማሪም በዘርፉ የነበሩ ማነቆዎችን በመለየት የተለየ መንገድ እንድንከተል የሚያስገድድ ነው ሲሉ ገልጸዋል፡፡

በዚህ ዘርፍ በ10 ዓመቱ ዕቅድ ውስጥ ለ5 ሚሊየን ዜጎች የስራ ዕድል ለመፍጠር መታቀዱም ተጠቁሟል፡፡

በመሳፍንት እያዩ