አዲስ አበባ፣ ሰኔ 8፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በቻይና ሀገር የሚመረተው የቮልስ ዋገን የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ በጊዜያዊነት ወደ ሀገር ውስጥ እንዳይገባ መታገዱን የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
በቻይና ሀገር ተገጣጥሞ ወደ ኢትዮጵያ እየገባ የሚገኘው ቮልስ ዋገን የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ሕጋዊ የሆነ ፈቃድ አለመኖሩን የጀርመኑ ኩባንያ በኤንባሲው በኩል በደብዳቤ ለሚኒስቴሩ ማሳወቁ ተገልጿል፡፡
በመሆኑም በቻይና ሀገር የሚመረተው የቮልስ ዋገን የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ከኩባንያው ሕጋዊ ፈቃድ ያለው መሆኑ እስከሚረጋገጥ ድረስ በጊዜያዊነት ወደ ሀገር ውስጥ እንዳይገባ መታገዱን ነው ሚኒስቴሩ ያስታወቀው፡፡
ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡ ተሽከርካሪዎች ላይ ክትትል በማድረግና የሕጋዊነት ማረጋገጫ መረጃዎችን የማጥራት ስራም በከፍተኛ ጥንቃቄ እየተሠራ መሆኑን ሚኒስቴሩ ገልጿል፡፡
መንግስት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች በስፋት እንዲመረቱ፣ እንዲገጣጠሙና ወደ ሀገር ውስጥ እንዲገቡ የተለያዩ ማበረታቻዎችን ለይቶ ተግባራዊ እያደረገ መሆኑን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል፡፡