አዲስ አበባ፣ሰኔ 16፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ሴት ዲፕሎማቶች በዓለም አቀፍ መድረኮች ያላቸውን ተሳትፎ በማጠናከር ሴቶችን በእኩልነት የምትወክል ፍትሃዊ ዓለም ለመፍጠር ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ጥሪ አቀረቡ።
ዓለም አቀፉ የሴት ዲፕሎማቶች ቀን “ሴቶች በዲፕሎሚሲው መስክ” በሚል መሪ ሀሳብ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተከብሯል፡፡
በመርሐ-ግብሩ ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ ፣የዓለም አቀፍ ተቋማት ሴት አመራሮች፣ ሴት ሚኒስትሮች፣ አምባሳደሮችና መቀመጫቸውን አዲስ አበባ ያደረጉ የተለያዩ ሀገራት ሴት ዲፕሎማቶች ተገኝተዋል።
ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ÷ሀገራቸውን በመወከል በተለያዩ ሀገራትና በዓለም አቀፍ ተቋማት በኃላፊነት ባገለገሉበት ወቅት ያሳለፉትን ልምድና ተሞክሮ አጋርተዋል።
በዚህም ወጣት ሴት ዲፕሎማቶች የሚገጥሟቸውን ጫናዎች በመቋቋም በመስኩ ውጤታማስራ ማከናወን እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡
በመሆኑም ሴት ዲፕሎማቶች በዓለም አቀፍ መድረኮች ያላቸውን ተሳትፎ በማጠናከር ፍትሃዊነት እንዲረጋገጥ ጠንክረው ሊሰሩ ይገባል ነው ያሉት፡፡
የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) በበኩላቸው÷ሴቶች በዲፕሎማሲው መስክ የማይተካ ሚና እንዳላቸው እና ከዚህ አኳያ መንግስት ሴቶች በሁሉም መልክ ያላቸው ተሳትፎ እንዲጎለብት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ÷ “በዲፕሎማሲው መስክ የሴቶችን ተሳትፎ በማጎልበት የተሻለች ዓለም ለመፍጠር ተግተን ልንሰራ ይገባል” ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!