የሀገር ውስጥ ዜና

የ12ኛ ክፍል ተፈታኞች ወደ ተመደቡበት ዩኒቨርሲቲ እየገቡ ነው

By ዮሐንስ ደርበው

July 24, 2023

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 17፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና የመጀመሪያ ዙር ተፈታኞች ወደተመደቡበት ዩኒቨርሲቲዎች እየገቡ ነው፡፡

ተፈታኞቹ ወደ ተመደቡበት ዩኒቨርሲቲ ማቅናት የጀመሩት ትናንት ሲሆን ዛሬም ቀጥሎ ውሏል፡፡

በጋምቤላ ክልል የ12ኛ ክፍል ፈተና የሚወስዱ ተማሪዎች ወደሚፈተኑባቸው ጋምቤላ ትምህርትና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ እና ጋምቤላ ዩኒቨርሲቲዎች ገብተዋል።

በክልሉ ፈተናውን በሠላማዊ መንገድ ለማስፈጸም የሚያስችል የቅድመ ዝግጅት ሥራ መጠናቀቁን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ መረጃ ያመላክታል፡፡

በተመሳሳይ አሶሳ ዩኒቨርሲቲ የተመደቡለትን የ12ኛ ክፍል ተፈታኞች ሲቀበል የዋለ ሲሆን÷ ለፈተና አስፈፃሚዎችም የፈተና ሂደት ገለፃ ተደርጓል፡፡

በወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ከሐምሌ 19 እስከ 28 ቀን 2015 ዓ.ም በሚካሄደው የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና በአስፈጻሚነት ለተመደቡ ፈታኝ መምህራን ገለጻ ተሰጥቷል።

እንዲሁም በጂንካ ዩኒቨርሲቲ የ2015 ዓ.ም 12ኛ ክፍል ማጠናቀቂያ ብሄራዊ ፈተና ለመፈተን የተመደቡ ተማሪዎች ተጠቃለው በመግባት ላይ መሆናቸው ተገልጿል።

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሚገኙ የማኅበራዊ ሣይንስ ተፈታኝ ተማሪዎችም ዛሬ ወደ ኮተቤ የትምህርት እና ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲዎች  ገብተዋል፡፡

የዘንድሮው የ12ኛ ክፍል የመጀመሪያ ዙር መልቀቂያ ፈተና ከሐምሌ 19 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ እንደሚሰጥ ይታወቃል፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!