የሀገር ውስጥ ዜና

በጃናሞራ ወረዳ በደረሰ የትራፊክ አደጋ የ9 ሰዎች ህይወት አለፈ

By Melaku Gedif

July 31, 2023

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 24፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በሰሜን ጎንደር ዞን ጃናሞራ ወረዳ በደረሰ የትራፊክ አደጋ የ9 ሰዎች ህይወት አለፈ።

አደጋው ከደባርቅ ከተማ ወደ ጃናሞራ 225 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ከ16 ሰዎች ጋር ጭኖ ሲጓዝ የነበረ የጭነት ተሽከርካሪ ከመንገድ ወጥቶ በመገልበጡ ነው የደረሰው።

በአደጋው እስካሁን የ9 ሰዎች ሕይወት ማለፉን የወረዳው ኮሙኒኬሽን ሃላፊ አቶ ገንታው ማሩ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ተናግረዋል።

ለህልፈት ከተዳረጉት በተጨማሪ በ4 ሰዎች ላይ ከባድ የአካል ጉዳት መድረሱን ጠቁመዋል፡፡

ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች አቅራቢያ ወደ ሚገኝ ሆስፒታል ተልከው የሕክምና ክትትል እየተደረገላቸው መሆኑንም  ገልጸዋል፡፡