ስፓርት

ማንቼስተር ዩናይትድ ከአዲዳስ ኩባንያ ጋር ትልቁን የመለያ ውል ተፈራረመ

By Mikias Ayele

July 31, 2023

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 24፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የእንግሊዙ እግር ኳስ ክለብ ማንቼስተር ዩናይትድ ከጀርመኑ ትጥቅ አምራች ኩባንያ አዲዳስ ጋር ለቀጣይ 10 ዓመታት ተጨማሪ ውል መፈራረሙን አስታወቀ።

በውሉ መሰረትም ማንቼስተር ዩናይትድ ከጀርመኑ ትጥቅ አምራች ኩባንያ ጋር ያላው የውል ሥምምነት እስከ ፈረንጆቹ ሰኔ 2035 ድረስ ይቆያል ነው የተባለው፡፡

በዚህም የላንክሻየሩ ክለብ ከኩባንያው ለ10 አመት የሚቆይ የ900 ሚሊየን ፓውንድ የመለያ ሥምምነት የተፈራረመ ሲሆን፥ ይህም የፕሪሚየርሊጉ ትልቁ የመለያ ገቢ በመሆን ተመዝግቧል፡፡

የክሉቡ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሪቻርድ አርኖልድ÷ “በማንቼስተር ዩናይትድ እና በአዲዳስ መካከል ያለው ግንኙነት አስደናቂ ከሚባሉት እና በዓለም ውስጥ ካሉ የኩባንያ እና ስፖርት ግንኑነቶች አንዱ ነው” ብለዋል፡፡

ክለቡ ከ1980ዎቹ ጀምሮ ከአዲዳስ ኩባንያ ጋር ግንኙነት እንደነበረው የገለፁት ስራ አስኪያጁ÷ ባለፉት አመታትትም አዲዳስ የተለያዩ ዲዛይን ያላቸው ትጥቆችን ሲያቀርብ መቆየቱን አስታውሰዋል፡፡

ማንቼስተር ዩናይትድ ከአዲዳስ ጋር ያደረገው ስምምነት ከክለቡ የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያለው ሲሆን፥ ክለቡ ሁለት ዓመታት ውስጥ በቻምፒየንስ ሊግ የማይሳተፍ ከሆነ ከአዲዳስ የሚያገኘው ዓመታዊ ክፍያ በ30 በመቶ ይቀንሳል ተብሏል።