የሀገር ውስጥ ዜና

ለችግር ተጋላጭ ለሆኑ ሴቶች የገቢ ማሰባሰብ ማስጀመርያ መርሐ ግብር ተካሄደ

By Shambel Mihret

August 17, 2023

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 11፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በተፈጥሮና በሰው ሰራሽ ምክንያት ለተለያዩ ችግር ተጋላጭ ለሆኑ ሴቶች የገቢ ማሰባሰብ ማስጀመርያ መርሐ ግብር በአዲስ አበባ ተካሂዷል፡፡

በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል በግጭትና በሌሎች ምክንያቶች ከኑሯቸውና ከሚተዳደሩበት ስራ የተፈናቀሉ ሴቶችን በገቢ ማስገኛ ዘርፍ እንዲሰማሩ ለማስቻል በተዘጋጀው የገቢ ማሰባሰቢያ ንቅናቄ መርሐ ግብር የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር)ን ጨምሮ ሌሎች የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡

መርሐ ግብሩ በዋናነት የታላቁ ሩጫን መሠረት ያደረገ ሲሆን ÷ ከዩ ኤን ዲ ፒ ጋር በመተባበር ለችግር ተጋላጭ የሆኑ ሴቶች በገቢ ማስገኛ ዘርፍ እንዲሰማሩ ለማስቻል ታልሞ የተዘጋጀ ነው ተብሏል፡፡

በዚሁ ወቅት ኤርጎጌ ተስፋዬ ዶ/ር)÷ተቋማቸው ለችግር ተጋላጭ የሆኑ ወገኖችን ህይወት በማሻሻል ለሀገራቸው አሻራቸውን ማሳረፍ እንዲችሉ እንዲሁም ከትሩፋቱ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ድጋፍ እንደሚያደርግ ጠቅሰዋል፡

የ ዩ ኤን ዲ ፒ ተወካይ ቱርሀን ሳላህ ÷ ሴቶች በጦርነት ምክንያት ግንባር ቀደም ተጠቂና ተጎጂ እንደሚሆኑ በመግለጽ መርሐ ግብሩም የተጎዱ ሴቶችን ለማቋቋም እንደሚረዳ አንስተዋል፡፡

የታላቁ ሩጫ መስራች አትሌት ሻለቃ ኃይሌ ገ/ስላሴ በበኩሉ÷ ይህ በግጭት ለተጎዳው የኢትዮጵያ ክፍል ታላቁ ሩጫ የሚያበረክተው ጥቂት አስተዋጽኦ ነው ማለታቸውን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል፡፡

በግጭቱ ከስራቸው ለተፈናቀሉና ብዙ ቤተሰብ ለሚያስተዳድሩ ሴቶች መነሻ ካፒታል በመስጠት በገቢ ማስገኛ መስኮች እንዲሰማሩ፣ ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን መደገፍ የሚችሉበትን አቅም ለመፍጠር በማሰብ ሃብት ለማሰባሰብ በትኩረት እየሰሩ በመሆኑ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያና ዩ ኤን ዲ ፒን አመስግነዋል፡፡