የሀገር ውስጥ ዜና

ኢትዮጵያ የኒውክሌር ኢነርጂን ለሰላማዊ ዓላማ ለመጠቀም ከሩሲያ ኩባንያዎች ጋር እየሰራች ነው

By ዮሐንስ ደርበው

September 20, 2023

አዲስ አበባ፣ መስከረም 9፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያ የኒውክሌር ኢነርጂን ለሰላማዊ መስክ ለመጠቀም የምታደርገው ጉዞ የተሳካና ደህንነቱ የተጠበቀ እንዲሆን ከሩሲያ ኒውክሌር ኢነርጂ ኩባንያዎች ጋር እየሰራች መሆኗ ተገለጸ፡፡

የኒውክሌር ሳይንስና ቴክኖሎጂ ማዕከልንና ብሔራዊ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ በኢትዮጵያ ለመገንባትና የኢትዮጵያን ብሔራዊ የኒውክሌር መሠረተ ልማት ለማልማት እየተሠራ ነው፡፡

በዚህም የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ከሩሲያ ሮሳቶም ኒውክሌር ኢነርጂ ኩባንያ ኃላፊዎች ጋር በአዲስ አበባ እየመከረ ነው፡፡

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ጽ/ቤት ኃላፊ ደስታ አበራ÷ ከሮሳቶም ጋር በመስራት የእውቀት፣ የልምድ እና የቴክኖሎጂ ሽግግርን በማሳለጥ ወደ ኒውክሌር ኢነርጂ ፕሮግራም ለሚደረገው ጉዞ መሠረት ነው ብለዋል፡፡

እንዲሁም ሥራው ደህንነቱ የተጠበቀ እና አካባቢን ያገናዘበ እንዲሆን በሁለትዮሽ ትብብር መሰራቱ ቅድሚያ የተሰጠው ተግባር ነው ማለታቸውን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል፡፡

ለሁለት ቀናት የሚቆየው መድረክ ከሩሲያ ኒውክሌር ኢነርጂ ኩባንያ የስራ ኃላፊዎች ሰፊና ጥልቅ የሆነ የእውቀት ቴክኖሎጂ ሽግግር ለማድረግ ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑ ታውቋል።

በሰላማዊ መንገድ አቶሚክ ኢነርጂ ግንባታና አጠቃቀም ላይ የተደረገው የሁለትዮሽ ትብብር በሀገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ ከሚያደርገው አስተዋጽኦ ባሻገር የኢትዮጵያ-ሩሲያ ግንኙነት ይበልጥ እያጠናከረው እንደሚሄድ ተጠቁሟል፡፡

#Ethiopia

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!