አዲስ አበባ፣ መስከረም 10፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) መልካም ዕሴቶችን ለመጠበቅና ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የወጣቶች ድርሻ የጎላ መሆኑን የወጣቶች ምክር ቤት ገለጸ፡፡
የዓለም የሰላም ቀን “የወጣቶች ንቁ ተሳትፎ ለዘላቂ ሰላም እና ለዓለም አቀፍ ግቦች” በሚል መሪ ሐሳብ በአዲስ አበባ እየተከበረ ነው፡፡
በመድረኩ ከተለያዩ አካባቢዎች የተውጣጡ ወጣቶች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንዲሁም የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ነው እየተከበረ ያለው፡፡
የወጣቶች ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ፉአድ ገና በአከባበሩ ላይ ባደረገው ንግግር÷ የሰላም መጉደል ሁሉንም የማሕበረሰብ ክፍል የሚጎዳ ቢሆንም በወጣቶች ላይ የሚኖረው ጉዳት ግን የከፋ ነው ብሏል።
መልካም ዕሴቶችን ለመጠበቅና ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የወጣቶች ድርሻ የጎላ መሆኑን ጠቁሞ÷ ለሀገር የሚተርፍ ሰላም እንዲኖር ወጣቱ የበኩሉን እንዲወጣ ፕሬዚዳንቱ ጥሪ አቅርቧል፡፡
ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ በሚከናወኑ ሥራዎችም የወጣቱን ሚና ለማላቅ በትኩረት እንደሚሠራም አመልክቷል።
የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ እታገኝ አሰፋ በበኩላቸው÷ ሰላምን ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ሥራዎችና የወጣቱ ንቁ ተሳትፎ ሁልጊዜም ሊተገበር የሚገባው ጉዳይ ነው ብለዋል፡፡
“ዓለም አቀፉ የሰላም ቀን” በፈረንጆቹ 1981 በመግሥታቱ ድርጅት መጽደቁን ተከትሎ በየዓመቱ መስከረም 10 ቀን ታስቦ ይውላል።
በይስማው አደራው
#Ethiopia
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!