አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 16፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ቻይና በፍልስጤም ጉዳይ ከሚመለከታቸው ወገኖች ሁሉ ግንኙነት እያደረገች እንደሆነ አስታወቀች።
የቻይና ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንዳስታወቀው፤ የመካከለኛው ቀውስ እንዲፈታ ቤጂንግ ያልተቋረጠ ጥረት ታደርጋለች።
ጥረቱ ውጤት እንዲያመጣምና የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲደረግ ከሚመለከታቸውና ወሳኝ ከሆኑ ወገኖች ጋር በመቀናጀትና በመተባበር የምትሰራ መሆኗን አመልክታለች።
በእስራዔልና በሀማስ መካከል ያለው ግጭት እንደቀጠለ ባለበት ሁኔታ የቻይና የመካከለኛው ምስራቅ ልዩ መልዕክተኛ ዣን ጁን ከሳዑዲ አረቢያ ባለስልጣናት ጋር ተገናኝተው መምከራቸውን አናዶሉ ዘግቧል።
የግጭቱ ሁኔታ አስከፊ መሆኑን የተናገሩት ልዩ መልዕክተኛው፤ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ንጹሃን ህይወታቸው በመቀጠፉ ሀገራቸው ቻይና ማዘኗን ገልጸዋል።
ከሳዑዲ አረቢያ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋሊድ አል-ኩራጂ በነበራቸው ቆይታም የመካከለኛው ምስራቅ ወቅታዊ ሁኔታ መሻሻል በሚችልበት ዙሪያ መምከራቸው ተጠቁሟል።