የሀገር ውስጥ ዜና

አቶ አደም ፋራህ ከጅቡቲ ወደብ የአፈር ማዳበሪያ የማጓጓዝ ሒደትን አስጀመሩ

By Melaku Gedif

November 02, 2023

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 22፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህ ለ2016/2017 ምርት ዘመን የአፈር ማዳበሪያ ከጅቡቲ ወደብ የማጓጓዝ ሒደትን ዛሬ አስጀምረዋል፡፡

በሥነ-ሥርዓቱ በግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) የተመራ ልዑክ እና የጅቡቲ መንግሥት የሥራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡

በግርማ አመንቴ (ዶ/ር) የተመራ ልዑክ ዛሬ ጠዋት በአፈር ማዳበሪያ የማጓጓዝ ሒደት ላይ በጅቡቲ የኢትዮጵያ አምባሳደር ብርሃኑ ፀጋዬ ጋር ተወያይተዋል፡፡

በውይይቱ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሣ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዋና ስራ አስፈፃሚ በሪሶ አመሎ (ዶ/ር)፣ የግብርና ሚኒስቴር እና የሌሎችም ተቋማት የስራ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል፡፡

ልዑኩ በቀጣይ ቀናት በጅቡቲ ቆይታው የአፈር ማዳበሪያ ዝውውር ማሻሻያ ጉዳዮች ላይ እንደሚመክር የኤምባሲው መረጃ ያመላክታል፡፡

የ2016/17 የምርት ዘመን ወደ ሀገር ውስጥ ከሚገባው የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ በመጀመሪያ ዙር 51 ሺህ 420 ሜትሪክ ቶን ዩሪያ የአፈር ማዳበሪያ የጫነች መርከብ ጥቅምት 18 ቀን 2016 ዓ.ም ጅቡቲ ወደብ መድረሷ ይታወሳል፡፡

#Ethiopia

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/ ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!