አዲስ አበባ፣ መጋቢት 18፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ባለፉት ስምንት ወራት የተከናወኑ የልማትና የመልካም አሥተዳደር ሥራዎች አበረታች መሆናቸውን የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ዋና አሥተዳዳሪ ወርቁ ኃይለማርያም ገለጹ፡፡
አቶ ወርቁ ዛሬ በሰጡት መግለጫ÷ ባለፉት ስምንት ወራት 500 ሺህ ሔክታር በሰብል በመሸፈን 14 ነጥብ 8 ሚሊየን ኩንታል ምርት መገኘቱን ገልጸዋል፡፡
እንዲሁም በተለያየ ችግር ምክንያት በመኸር ወቅት ያልተሳኩ ተግባራትን በበጋ መስኖ ልማት ለማካካስ 43 ሺህ ሔክታር በማልማት 1 ነጥብ 8 ሚሊየን ኩንታል ምርት ለማግኘት እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡
በተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ተግባራት አበረታች ውጤት ለማምጣት እየተሠራ መሆኑን በመግለጽ÷ ለመጪው ክረምት 440 ሚሊየን ችግኞችን በማዘጋጀት የፍራፍሬና ደን ልማትን ለማጠናከር ታቅዶ እየተሰራ እንደሆነም አመላክተዋል፡፡
የሥራ ዕድልንና የልማት ተግባራትን ለማሳደግ የተከናወነው ሥራ ውጤታማ መሆኑን አንስተው÷ 7 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ካፒታል ላስመዘገቡ 57 ባለሀብቶች ፈቃድ መሰጠቱን ተናግረዋል፡፡
በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተግባራት የማኅበረሰቡን ጥያቄዎች ለመመለስ ጥረት ሲደረግ መቆየቱን አስረድተው÷ ከመልካም አሥተዳደር ችግሮች አኳያም ግልፅነትና ተጠያቂነት ያለው አሰራርን ለማጠናከር እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡
በሙሉጌታ ደሴ