የሀገር ውስጥ ዜና

አሜሪካ ተቀምጠው የኢትዮጵያን ሰላም የሚያውኩ ተፈላጊዎችን ሀገሪቱ አሳልፋ በመስጠት ትብብር እንድታደርግ ተጠየቀ

By Melaku Gedif

May 10, 2024

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 2፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋን በቢሮአቸው ተቀብለው አነጋግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ከአሜሪካው የፌዴራል የምርመራ ቢሮ (ኤፍቢአይ) ጋር ያለውን ግንኙነት የበለጠ ለማጠናከር አምባሳደሩ የበኩላቸውን ሚና እንዲጫወቱ ኮሚሽነር ጀነራል ጥሪ አቅርበዋል፡፡

በተለይ በአሜሪካ ተቀምጠው የኢትዮጵያን ሰላምና ደኅንነት የሚያውኩ ተፈላጊዎችን አሳልፎ በመስጠት ዙሪያ ትብብር እንዲያደርጉም ጠይቀዋል፡፡

አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ በበኩላቸው÷ በአሜሪካን መንግሥት የሚፈለጉ ወንጀለኞችን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ አሳልፎ በመስጠት ላበረከተው አስተዋፅኦ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

ሀገራቸው ለኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ተመሳሳይ ድጋፎችን እንድታደርግ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንደሚያደርጉ መናገራቸውንም የፌደራል ፖሊስ መረጃ አመልክቷል፡፡