አዲስ አበባ፣ ሰኔ 1፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአንጋፋው አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤት በአሸናፊ ከበደ (ፕ/ር) ስም የሰየመውን የሙዚቃዊ ጥበባት ማዕከል መርቀዋል፡፡
የሙዚቃዊ ጥበባት ማዕከሉ በኢትዮጵያ በአይነቱ የመጀመሪያ መሆኑን የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መረጃ ያመላክታል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት፥ሙዚቃ ኃይል አለው፤ ይህን ኃይል ለወጣቶቻችን አብርሆት ልንጠቀምበት ይገባል ብለዋል፡፡
ጥበባት መጪውን ትውልድ ቅርጽ በማስያዝና የከተማችንን የቱሪዝም መስሕብ በማላቅ ከፍ ያለ ሚና እንደሚጫወቱ ጠቅሰው፥ይህን አቅም በምሉዕነት መጠቀም እንደሚገባ አስገንዝበዋል።