የሀገር ውስጥ ዜና

የኢትዮጵያ እና ፈረንሳይን ግንኙነት ለማጠናከር ያለመ ምክክር ተደረገ

By ዮሐንስ ደርበው

December 21, 2024

አዲስ አበባ፣ ታሕሣሥ 12፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በኢትዮጵያ እና ፈረንሳይ መካከል ያሉ ዘርፈ-ብዙ ትብብሮችን በይበልጥ ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ከፕሬዚዳንት ማክሮን ጋር መምከራቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡

ከፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ጋር በብሔራዊ ቤተ-መንግሥት የሁለትዮሽ ውይይት ማድረጋቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው አስፍረዋል፡፡

በውይይታቸውም ሰፋ ያለ መጠነ-ርዕይ ባላቸው የሁለትዮሽ እና ባለብዙ ወገን ጉዳዮች ላይ መምከራቸውን ነው የገለጹት፡፡

ፕሬዚዳንቱ እና የፈረንሳይ መንግሥት ለብሔራዊ ቤተ መንግስት እና በመካሄድ ላይ ባለው የላሊበላ ውቅር አብያተ-ክርስቲያናት እድሳት ሥራዎች ላደረጉት አስተዋፅዖም ምሥጋና አቅርበዋል፡፡

በውይይታችን በተለያዩ ዘርፎች የሚኖሩ ትብብሮችን ፈትሸናል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ÷ ለአብነትም የፈረንሳይን ኢንቨስትመንት መጨመር ብሎም በትምህርት እና ባሕል ዘርፎች ያለንን ግንኙነት ለማጠናከር ባለሙ ጉዳዮች ላይ ተነጋግረናል ነው ያሉት።

በተጨማሪም ታሪካዊ ትስስራችንን በይበልጥ የመገንባት አስፈላጊነትን በውይይታችን አፅንዖት ሰጥቼ አንስቻለሁ ብለዋል።