የሀገር ውስጥ ዜና

በኢትዮጵያ ከአድሏዊነት ነፃ የሆነ አገልግሎት የሚሰጥበት ሥርዓት ተዘርግቷል – አቶ መሐመድ እድሪስ

By ዮሐንስ ደርበው

February 24, 2025

አዲስ አበባ፣ የካቲት 17፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በኢትዮጵያ ከአድሏዊነት ነፃ የሆነ አገልግሎት የሚሰጥበት ሥርዓት ተዘርግቷል ሲሉ የሰላም ሚኒስትር መሐመድ እድሪስ ገለጹ።

የሰላም ሚኒስትሩ በሞሮኮው መሐመድ 6ኛ ፋውንዴሽን ሴክሬታሪ መሐመድ ረፊቅ (ዶ/ር) ከተመራ ልዑክ ጋር የሁለቱን ሀገራት መልካም ግንኙነትና ትብብር ማጠናከር በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ውይይት አድርገዋል፡፡

ልዑኩ ኢትዮጵያ ቀደምት ስልጣኔ ያላት ጥንታዊት ሀገር እንደመሆኗ ብዙ ልምዶችን ማካፈል እንደምትችል በማሰብ ለልምድ ልውውጥ መምጣቱ ተነግሯል።

ኢትዮጵያ ሁሉንም ሃይማኖቶችና እምነቶች በእኩልነትና ፍትሐዊነት የምታስተናግድበት ሕገ መንግሥት መኖሩን አቶ መሐመድ አስታውሰዋል።

ከአድሏዊነት ነፃ የሆነ የመንግሥት አገልግሎት የሚሰጥበት ሥርዓት ተዘርግቷል በማለት ገልጸው፤ ይህም ሃይማኖቶችና እምነቶች በመካከላቸው ሰላማዊ የሆነ ግንኙነት ማጠናከሩን ተናግረዋል።

በ48 የአፍሪካ ሀገሮች ቅርንጫፎችን የከፈተው የሞሮኮ መሐመድ 6ኛ ፋውንዴሽን በኢትዮጵያም ቅርንጫፍ ለመክፈት በልጹኩ በኩል ላቀረበው ጥያቄ፤ ወደ ፊት ምላሽ የሚሰጥ መሆኑን መግለጻቸውን የሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ አመላክቷል፡፡

ልዑካኑ በበኩላቸው፤ በብዝኃነት አያያዝ በተለይም ቤተ እምነቶች በሰላም እና በአብሮነት ለጋራ ሰላም እና ተጠቃሚነት የሚሠሩበት ሁኔታ ለሀገራቸው ጥሩ ልምድ እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡