የሀገር ውስጥ ዜና

ከ128 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የተገነባው የመስኖ ፕሮጀክት ተመረቀ

By Adimasu Aragawu

May 06, 2025

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 28፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከ128 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የተገነባው የወልዲያ አረዳ መካከለኛ የመስኖ ፕሮጀክት ተመርቋል።

ፕሮጀክቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) እና የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር ኢ/ር) በይፋ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል።

የመስኖ ፕሮጀክቱ የአርሶ አደሮችን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት በማሳደግና ገበያ በማረጋጋት ያለው ፋይዳ ከፍ ያለ መሆኑ ተገልጿል።

2 ሺህ 850 ሜትር ዋና ካናል እና 3 ሺህ 100 ሜትር መለስተኛ ካናል በድምሩ 5 ሺህ 950 ሜትር ርዝመት ያለው የካናል ግንባታ እና 5 ሺህ ኪዩቢክ ሜትር ውሃ መያዝ የሚችል የገንዳ ሥራ እንደተሰራም ተመላክቷል።

በተመሳሳይ በዛሬው ዕለት 120 ሜትር ርዝመት ያለው በሶዶ ወረዳ የሻሾ ወንዝ ተንጠልጣይ ድልድይ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።

ድልድዩ ከ7 ነጥብ 4 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ እንደተደረገበት የተገለጸ ሲሆን÷ ለሰዎችና ለእንስሳት አገልግሎት ምቹ እንዲሆን ተደርጎ የተገነባ መሆኑም ተገልጿል።

በኦሊያድ በዳኔ