የሀገር ውስጥ ዜና

ሰመራ ከተማን በጋራ ለማልማት ያለመ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ-ግብር ተጀመረ

By ዮሐንስ ደርበው

May 07, 2025

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 29፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የአፋር ክልል ርዕሰ መሥተዳድር አወል አርባ “ሰመራ ከተማን በጋራ እናልማ“ በሚል መሪ ሐሳብ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ-ግብርን አስጀምረዋል፡፡

የክልሉ ኮንስትራክሽን እና ከተማ ልማት ቢሮ ኃላፊ አሕመድ ኑር ሳሊም (ኢ/ር)፤ ሰመራ ለቀጣዩ ትውልድ ምቹ እንድትሆን የ1ኛው ዙር የኮሪደር ልማት ፕሮጀክት በክልሉ በጀት መጀመሩን እና በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል፡፡

ለፕሮጀክቱ ማስፈፅሚያ ተጨማሪ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ-ግብር ማካሄድ አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱንም ለፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ተናግረዋል፡፡

ትውልደ ኢትዮጵያውያን፣ የአካባቢው ተወላጆች እና ነዋሪዎች “ሰመራ ከተማን በጋራ እናልማ“ ተብሎ በተዘጋጀው መርሐ-ግብር በንቃት እንዲሳተፉም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

ገንዘቡን በቴሌ ብር እና በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተከፈቱ አካውንቶች ገቢ ማድረግ እንደሚቻልም ጠቁመዋል፡፡

በተጨማሪም በቅርቡ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ-ግብር (ቴሌቶን) እንደሚካሄድ ነው ያመላከቱት፡፡

የሰመራ-ሎግያ ከተማ አሥተዳደር ከንቲባ አብዱ ሙሳ በበኩላቸው፤ ሰመራን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ እየተከናወነ ባከለው ሥራ በርካታ የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡

በአሊ ሹምባሕሪ