አዲስ አበባ፣ ግንቦት 4፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የዜጎችን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ኢትዮጵያ በነጻ እንዲቀርብ ያደረገችው የኮደርስ ስልጠና ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ የሚጠይቅ መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር አማካሪ አብዮት ባዩ (ዶ/ር) አስገነዘቡ፡፡
የ5 ሚሊየን የኢትዮጵያ ኮደሮች ፕሮግራም ወጣቶች የዲጂታል ክህሎት ኖሯቸው በዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ ትርጉም ያለው ተሳትፎ እንዲያደርጉ ያስችላል ብለዋል አማካሪው፡፡
የሚሰጡ ስልጠናዎችም፤ በፕሮግራሚንግ፣ በዳታ ሳይንስ እና በአርተፊሻል ኢንተሊጀንስ ላይ የሚያተኩሩ መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡
በተለያዩ የሥራ መስኮች አዳዲስ ዕድሎችን ለመፍጠር፣ አሁን እየተሠሩ ያሉ ሥራዎችን በዲጂታል ለመደገፍ እና ተወዳዳሪ ለመሆን ስልጠናው እንደሚያግዝም ለፋና ዲጂታል ተናግረዋል፡፡
እነዚህን ስልጠናዎች ግለሰቦች በውጭ ምንዛሪ ክፍያ በመፈጸም የሚያገኟቸው መሆናቸውን ገልጸው፤ ይህ ለአብዛኛው የሀገራችን ወጣት አዳጋች መሆኑን በመገንዘብ መንግሥት በነጻ ማቅረቡን አስታውቀዋል፡፡
ኢትዮጵያውያን ወጣቶችም ዕድሉን በነጻ እንዲጠቀሙ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
በዮሐንስ ደርበው