የሀገር ውስጥ ዜና

በጤና ዘርፍ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመፍታት የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ – ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)

By Yonas Getnet

June 02, 2025

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 25፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በጤናው ዘርፍ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመፍታት የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ አሉ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)፡፡

በክልሉ ከጤና ባለሙያዎች ጋር “የጤና ዘርፍ አርበኝነት ለሀገር ዕድገት” በሚል መሪ ሃሳብ ክልል አቀፍ የማጠቃለያ ውይይት እየተካሄደ ነው።

ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት ÷ መንግስት በጤናው ዘርፍ የሚስተዋሉ ችግሮችን እና የጤና ባለሙያውን ጥያቄ ለመፍታት ባለፉት ዓመታት በርካታ ሥራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል፡፡

በዘርፉ እየተከናወኑ ባሉ የሪፎርም ሥራዎች ለውጦች መመዝገባቸውን ጠቁመው÷ በቀጣይ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመፍታት የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል፡፡

የጤና ባለሙያዎች ለሙያቸው የገቡትን ቃል በማክበር ሕዝባቸውን እያገለገሉ መሆኑን ጠቅሰው÷ ጥያቄያቸውን ጠልፈው የፖለቲካ መጠቀሚያ ለሚያደርጉ አካላት ራሳቸውን አሳልፈው መስጠት እንደሌለባቸው አስገንዝበዋል።

በጤናው ዘርፍ የሚነሱ ችግሮችን ለመፍታት እና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት በትኩረት እንደሚሰራም ርዕሰ መስተዳድሩ አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡

በፍሬው ዓለማየሁ