የሀገር ውስጥ ዜና

በኦሮሚያ ክልል በባህል ልማት የተከናወኑ ሥራዎች በተሞክሮነት የሚወሰዱ ናቸው – ወ/ሮ ሸዊት ሻንካ

By Melaku Gedif

June 09, 2025

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 2፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በኦሮሚያ ክልል በባህል ልማት ላይ የተሰራው ሥራ ልምድ ሊወሰድበት የሚገባ ነው አሉ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ።

ሚኒስትሯን ጨምሮ ሌሎች የሚኒስቴሩ እንዲሁም የኦሮሚያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊዎች በሸገር ከተማ የተከናወኑ የባህል ልማት ሥራዎችን ተመልክተዋል።

ወ/ሮ ሸዊት ሻንካ በዚህ ወቅት እንደገለጹት÷ በክልሉ የተከናወኑ የባህል ልማት ሥራዎች ልምድና ተሞክሮ የሚሰድባቸው ናቸው።

በተለይም ባህላዊ ፍርድ ቤቶችን ወደ ሥራ በማስገባት ህብረተሰቡ በወግና ባህሉ መሰረት ፍትሕ ማግኘት መቻሉን አስረድተዋል።

ባህላዊ ፍ/ቤቶቹ ግጭቶችና አለመግባባቶች እንዲፈቱና ዘላቂ እርቅና ሰላም እንዲወርድ እያደረጉ መሆኑን መገንዘባቸውን አንስተዋል።

ማህበረሰቡ በራሱ ባሕል፣ ሥርዓትና ዕሴት ጉዳዩ ታይቶ በአካባቢው ባህልና ወግ መሰረት ውሳኔ እያገኘ እንደሚገኝም አብራርተዋል፡፡

በአጠቃላይ ሸገር ከተማን ጨምሮ በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በባህል ልማት ላይ እየተሰራ ያለው ሥራ እንደ ልምድ ወደ ሌሎች አካባቢዎች መስፋፋት ያለበት ነው ብለዋል።

የኦሮሚያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ጀሚላ ሲምቢሩ በበኩላቸው÷ የክልሉ መንግስት ለባህል ልማት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

በእስካሁኑ ሒደትም ከገዳ ሥርዓት የመነጩ ባህላዊ እሴቶችን በማጎልበት ህብረተሰቡ በሚያውቀው ባህልና ወግ አገልግሎት ማግኘት እንዲችል እየተደረገ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል።

በተለይም ባህላዊ ፍ/ቤቶች ሕብረተሰቡ በአካባቢውና በሚያውቀው አባ ገዳዎች፣ ሃዳ ሲንቄዎችና ሀገር ሽማግሌዎች መዳኘቱ ፍትሕን በቅርበት እና በፍጥነት እንዲያገኝ አስችሎታል ብለዋል።

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡- YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook FBC (Fana Broadcasting Corporate S.C.) Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook WMCC TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Documentary YouTube www.youtube.com/@fanamcdocumentary በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን