የሀገር ውስጥ ዜና

በአፋር ክልል ከ124 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በግብርና ለምቷል – አቶ አወል አርባ

By Yonas Getnet

July 21, 2025

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 14፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በአፋር ክልል ከ124 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በግብርና ለምቷል አሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ፡፡

አቶ አወል በክልሉ ም/ቤት 6ኛ ዙር 4ኛ የሥራ ዘመን 8ኛ መደበኛ ጉባዔ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት እንዳሉት ÷ በክልሉ በግብርና ዘርፍ በተከናወነ ሥራ ከ124 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት ማልማት ተችሏል።

በ2017 በጀት ዓመት 4 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል ምርት መሰበሰቡን ጠቁመው÷ በዚህም የእቅዱን 93 ነጥብ 3 በመቶ ማሳካት መቻሉን ጠቅሰዋል።

በአረንጓዴ አሻራ 10 ሚሊየን ችግኝ ለመትከል ታቅዶ የዕቅዱን 93 ነጥብ 9 በመቶ ማሳካት ተችሏል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ ÷ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶች ላይ ውጤታማ ሥራ መከናወኑን ተናግረዋል።

በመኖ ልማት ከዚህ በፊት 2 ሺህ ሔክታር ብቻ ሲለማ እንደነበረ እና አሁን ላይ ወደ 25 ሺህ ሔክታር ማድረስ መቻሉን ጠቅሰው ÷ በተከናወነው ሥራም 362 ሺህ ቶን በላይ መኖ መመረቱን አመልክተዋል፡፡

በሌማት ትሩፋት መርሐ ግብር የክልሉ የወተት ምርት ከለውጥ በፊት ከነበረው 49 ነጥብ 9 ሚሊየን ሊትር ወደ 391 ሚሊየን ሊትር ማደጉን ነው ያስረዱት፡፡

በበጀት ዓመቱ 158 ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው ወደ ሥራ መግባታቸውን የተናገሩት አቶ አወል ÷ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ 6 ፋብሪካዎች ሥራ መጀመራቸውን አብራርተዋል፡፡

በሌላ በኩል ከ130 ኪሎ ሜትር በላይ የመንገድ ግንባታ እና 480 ኪሎ ሜትር የመንገድ ጥገና ሥራ መከናወኑን ነው የገለጹት፡፡

በከሊፋ ከድር