የሀገር ውስጥ ዜና

ኢትዮጵያና ፓኪስታን የአየር ንብረት ለውጥን በጋራ ለመከላከል ተስማሙ

By Adimasu Aragawu

July 29, 2025

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 22፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በፓኪስታን የኢትዮጵያ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ጀማል በከር (ዶ/ር) ከፓኪስታን የፔትሮሊየምና የአየር ንብረት ለውጥ ሚኒስትር ሙሳዲክ ማሱድ ማሊክ (ዶ/ር) ጋር ተወያይተዋል።

በውይይታቸውም ሁለቱ ሀገራት በአየር ንብረት ለውጥ እና አካባቢ ጥበቃ ላይ ያላቸውን የሁለትዮሽ ግንኙነትና ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ መክረዋል።

አምባሳደር ጀማል በከር (ዶ/ር) በዚህ ወቅት÷ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን ተጽዕኖ ለመቋቋም እያከናወነቻቸው ስላሉ ተግባራት ገለጻ አድርገዋል።

በተለይም በአረንጓዴ አሻራ ንቅናቄ የኢትዮጵያን ደን ሽፋን ከማሳደግና የአፈር መሸርሸር ችግርን ከመቅረፍ ባለፈ ብዝኃ ሕይወትን በመጠበቅና የአየር ንብረት ለውጥን በመቋቋም ረገድ ትልቅ ፋይዳ ያለው ሥራ መሰራቱን አንስተዋል።

ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ መድረኮች ለተለያዩ ሀገራት ድምፅ በማሰማት የአየር ንብረት ፍትሕ እንዲሰፍንና የበለጸጉ ሀገራት የገቡትን ቃል እንዲያከብሩ በጽናት እየሰራች እንደምትገኝም ተናግረዋል።

ሙሳዲክ ማሱድ ማሊክ (ዶ/ር) በበኩላቸው÷ የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ ንቅናቄ እጅግ አስደናቂና ለሌሎች አርአያነት ያለው ተሞክሮ መሆኑን ገልጸዋል።

ፓኪስታን በአየር ንብረት ለውጥ ከፍተኛ ጉዳት ከሚደርስባቸው ሀገራት አንዷ መሆኗን ጠቅሰው÷ የኢትዮጵያን ስኬታማ ተሞክሮ ለመውሰድ ዝግጁ መሆናቸውን ጠቁመዋል።

በዚህም ከኢትዮጵያ ኤምባሲ ጋር በመተባበር የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብርን በፓኪስታን ለመተግበር ያላቸውን ቁርጠኝነትና ጠንካራ ፍላጎት ማረጋገጣቸውን ኤምባሲው ለፋና ዲጂታል በላከው መረጃ አመላክቷል።

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Documentary YouTube www.youtube.com/@fanamcdocumentary በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!