የሀገር ውስጥ ዜና

ጣና ነሽ ፪ ከመነሻዋ እስከ መድረሻዋ የታየው ድንቅ አቀባበል የታሪካችን አካል ሆኖ ተመዝግቧል

By sosina alemayehu

August 01, 2025

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 25፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው ጣና ነሽ ፪ ከመነሻዋ እስከ መድረሻዋ የታየው ድንቅ አቀባበል የታሪካችን አካል ሆኖ ተመዝግቧል አሉ።

ከጅቡቲ ዶራሌ ወደብ መጋቢት 30 ቀን 2017 ዓ.ም የተነሳችው ጣና ነሽ ፪ ጀልባ በዛሬው ዕለት የየብስ ጉዞዋ መጨረሻ ወደ ሆነው ባህር ዳር ከተማ ስትደርስ ደማቅ አቀባበል ተደርጎላታል።

በአቀባበል ሥነ ሥርዓቱ ላይ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው እንዳሉት፤ ጣና ነሽ ፪ የኢትዮጵያውያን የአንድነት እና የአብሮነት ማሳያ ምስጢር ሆናለች።

ከጅቡቲ ወደብ ተነስታ ባሕር ዳር እስክትደርስ የታዩ ክስተቶች የዚህ ማሳያ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለወራት በተደረገው የጀልባዋ ጉዞ አስተዋጽኦ ለነበራቸው ሁሉ ምስጋና አቅርበዋል።

ጣና ነሽ ፪ በደረሰችበት ሁሉ በፍቅር እየተቀበሉ በፍቅር የሸኟት ኢትዮጵያውያን ሃብት ናት ብለዋል።

ጣና ነሽ ፪ ከመነሻዋ እስከ መድረሻዋ የታየው ድንቅ አቀባበል የአብሮነታችን፣ የአንድነታችን ደማቅ ምልክት እና የታሪካችን አካል ሆኖ ተመዝግቧል ነው ያሉት።