አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 29፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በተጠናቀቀው የ2017 በጀት ዓመት የጊቤ ሦስት የኃይል ማመንጫ ግድብ በፈጠረው ሰው ሰራሽ ሐይቅ 3 ሺህ 210 ቶን የዓሣ ምርት ተገኘ።
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል የዳውሮ ዞን ግብርና መምሪያ የእንስሳትና ዓሣ ሃብት ልማት ዘርፍ ኃላፊ አስፋው ጮራሞ ለፋና ዲጂታል እንዳሉት÷ በዞኑ ከኩሬ እና ከተለያዩ ውሃ አካላት 4 ሺህ 200 ቶን የዓሣ ስጋ ለማምረት ታቅዶ 4 ሺህ 111 ነጥብ 6 ቶን ዓሳ ተመርቷል።
ከዚህ ውስጥ 3 ሺህ 210 ቶን ምርት የተገኘው የጊቤ ሦስት የኃይል ማመንጫ ግድብ ከፈጠረው ሰው ሰራሽ ሐይቅ ነው ብለዋል።
በሐይቁ ላይ 160 ወጣቶች በተለያዩ ማህበራት ተደራጅተው በዓሣ ማምረት ስራ ላይ የተሰማሩ መሆኑን ተናግረዋል።
ለወጣቶቹ ምርታማነታቸው እንዲጨምር የሚያስችል ድጋፍ እየተደረገላቸው እንደሆነ ጠቅሰው÷ የምርት ማከማቻና መሸጫ ሼድ ግንባታ፣ የምርት ማቆያ ፍሪጆች እና ሐይቅ ላይ የምርት ማጓጓዣ የሞተር ጀልባ እንዲያገኙ ተደርጓል ነው ያሉት።
እንዲሁም ምርትን ወደ ተለያዩ የአካባቢ ገበያዎች አጓጉዘው የሚሸጡበት ፍሪጅ የተገጠመለት መኪና እና ሌሎች ድጋፍ መደረጋቸውን ገልጸዋል።
ወጣቶቹ በቀን እስከ አንድ ቶን የሚደርስ ዓሣ እያመረቱ መሆናቸውን ገልጸው÷ ከአካባቢ ገበያ ጀምሮ እስከ ማዕከላዊ ገበያ ድረስ ምርት እያቀረቡ እንደሚገኙ አስረድተዋል።
በሐይቁ ውስጥ የተለያዩ የዓሣ ዝርያዎች እንዳሉም አቶ አስፋው ጠቁመዋል።
የጊቤ ሦስት የኃይል ማመንጫ ግድብ 1 ሺህ 870 ሜጋ ዋት ኤሌክትሪክ በማመንጨት ከታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ቀጥሎ ግዙፉ የኃይል ማመንጫ ሲሆን÷ ግድቡን ተከትሎ የተገነባው የሀላላ ሎጅም ለአካባቢው የቱሪስት መዳረሻ በመሆን የገቢ ምንጭ ሆኖ እያገለገለ ይገኛል።
በአድማሱ አራጋው
ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Documentary YouTube www.youtube.com/@fanamcdocumentary በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!