አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 29፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከ5 ሺህ በላይ የትምህርት ቤት አመራሮችና መምህራን የአቅም ማጎልበቻ ስልጠና እየወሰዱ ነው አለ የክልሉ ትምህርት ቢሮ።
የቢሮው ምክትልና የትምህርት ልማት ዘርፍ ኃላፊ አቶ አስከብር ወልዴ ለፋና ዲጂታል እንዳሉት÷ የሀገሪቱን የትምህርት ሥርዓት ሪፎርም ተከትሎ በዘርፉ ያሉ ችግሮችን ለመለየት በተደረጉ ጥናቶች የመምህራን አቅም ላይ ክፍተቶች እንዳሉ ማረጋገጥ ተችሏል።
በዚህም የመምህራን እና ትምህርት ቤት አመራሮች የክህሎት ክፍተት ለመሙላት የሚያስችሉ የስልጠና መርሐ ግብሮች እየተከናወኑ ይገኛል ብለዋል።
የተለያዩ ሞጁሎችን እና ማንዋሎችን የማዘጋጀት እንዲሁም አሰልጣኝ መምህራንን በመለየት አሁን ላይ በክልሉ ከ5 ሺህ በላይ መምህራንና የትምህርት ቤት አመራሮች ስልጠና እየወሰዱ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
ስልጠናው መምህራን በሚያስተምሩት የትምህርት ዓይነት ተገቢ ዕውቀት እንዲሁም ተጨማሪ አቅምና ክህሎት እንዲኖራቸው፣ የማስተማር ሥነ ዘዴያቸውን እንዲያሳድጉ እና ቴክኖሎጂን ለመማር ማስተማር ስራ እንዲጠቀሙ የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል።
ይህም መምህራን ብቁ ሆነው በተገቢው መንገድ ዕውቀታቸውን ለተማሪዎቻቸው ማስተላለፍ የሚችሉበትን ዕድል እንደሚፈጥር ጠቅሰው÷ በዚህም የትምህርት ጥራትና የተማሪዎችን ውጤት ከማሻሻል አንጻር ትልቅ ውጤት ይጠበቃል ብለዋል።
በተጨማሪም ለትምህርት ቤት አመራሮች መሰረታዊ የመማር ማስተማር አመራርነት ላይ መሰረታዊ የክህሎት ስልጠና እየተሰጠ መሆኑን ጠቁመዋል።
መምህራን በሀገሪቱ የትምህርት ዘርፍ የተማሪዎች ውጤት እና የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል የማይተካ ሚና እንዳላቸው የገለጹት አቶ አስከብር÷ መምህራንን ማሰልጠን፣ ማብቃትና ወደ ስራ ማሰማራት እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል።
በዮናስ ጌትነት
ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡- YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Documentary YouTube www.youtube.com/@fanamcdocumentary በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!