የሀገር ውስጥ ዜና

አረንጓዴ አሻራ ለትውልድ ምቹ ሀገርን የመገንባት ትልቅ ተነሳሽነት ነው

By Melaku Gedif

August 08, 2025

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 2፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የአረንጓዴ አሻራ ለትውልድ ምቹ ሀገርን የመገንባት ትልቅ ተነሳሽነት በመሆኑ ተሳትፏችንን አጠናክረን እንቀጥላለን አሉ የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች።

በኦሮሚያ ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አባላት በሸገር ከተማ መነ አብቹ ክፍለ ከተማ የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር አካሂደዋል።

የክልሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ም/ቤት ዋና ሰብሳቢ ሰለሞን ታፈሰ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ አረንጓዴ አሻራ ለትውልዱ የተሻለችና ምቹ ሀገርን የመገንባት አጀንዳ በመሆኑ ሁሉም ዜጋ በንቃት ሊሳተፍ ይገባል፡፡

የጋራ በሆኑ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በጋራ መሰለፍ ይገባል ያሉት ሰብሳቢው፥ ለአብነትም በልማት፣ በሰላም እና የሀገርን ሁለንተናዊ እድገት ማረጋገጥ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ በጋራ መሰለፍ እንደሚያስፈልግ ጠቅሰዋል፡፡

መንግስት የተፎካካሪ ፓርቲዎች በዚህ ሒደት እንዲሳተፉ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ነው ያስገነዘቡት፡፡

በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ኃላፊ ሞገስ ኢደኤ በበኩላቸው÷ አረንጓዴ አሻራ የፖለቲካ አመለካከት ልዩነት የማይገድበው የጋራ ሀገራዊ አጀንዳ ነው ብለዋል።

የፖለቲካ ፓርቲዎች አረንጓዴ አሻራን ጨምሮ በሀገራዊ ጉዳዮች ተቀራርበው መስራታቸው ለሀገር እድገትና ለዴሞክራሲ ባህል መዳበር አጋዥ መሆኑን ጠቅሰዋል።

በኦሮሚያ ክልል የፓለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክርቤት ፀሐፊ ታሪኩ ድንበሩ ፥ አረንጓዴ አሻራ ነገን የተሻለ ለማድረግ ትልቅ ተነሳሽነት መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል።

የገዳ ሥርዓት ለኦሮሞ ነፃነት ፓርቲ ፕሬዚዳንት ሮበሌ ታደሰ ፥ አረንጓዴ አሻራ የአንድ ፓርቲ ጉዳይ ሳይሆን የሁሉም ጉዳይ በመሆኑ ተሳትፏችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ነው ያሉት።

አረንጓዴ አሻራን ጨምሮ በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የሚያደርጉትን ተሳትፎ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ የተናገሩት ደግሞ በኦሮሚያ ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሥራ አስፈፃሚ አባል ኤርሚያስ ተገኔ ናቸው።

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Documentary YouTube www.youtube.com/@fanamcdocumentary በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!