አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 5፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ በሥነ ምግባሩ የተመሰገነ አገልጋይ የሰው ኃይል ለመፍጠር የሚደረገው ጥረት ቀጥሏል አሉ።
ጉምሩክ ኮሚሽን ከሁሉም የሀገሪቱ ክፍሎች የተውጣጡ ከ3 ሺህ 300 በላይ ለሆኑ አዳዲስ ሰልጣኝ ሰራተኞች የአቀባበል ሥነ ሥርዓት በሚሊኒየም አዳራሽ አካሂዷል።
በሥነ ሥርዓቱ ላይ ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የምትፈልገውን አይነት በሥነ ምግባሩ የተመሰገነ አገልጋይ ለመፍጠር ጥረት እየተደረገ ይገኛል።
የጉሙሩክ ኮሚሽንም የድርሻውን ለመወጣት እና ተልዕኮውን ለማሳካት የሚያስችል አገልጋይ ለመፍጠር የበኩሉን እየተወጣ እንደሆነ አመልክተዋል።
ሰልጣኝ ሰራተኞቹ የሚሰጣቸውን ሀላፊነት ለመወጣት እንዲችሉ በሚወስዱት ቅድመ ስልጠና የሚጠበቅባቸውን ሁሉ በአግባቡ እንዲወጡ አሳስበዋል።
የማሰልጠን ሂደቱን የሚረከበው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ሰልጣኞቹ በዕውቀትና በክህሎት የተሟላ አቅም እንዲያገኙ ለማስቻል ዩኒቨርሲቲው ዝግጁ ነው ብለዋል።
በዳዊት ጎሳዬ