አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 16፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በአዲስ አበባ ከተማ የተገነቡ የገበያ ማዕከላት፣ የመኪና ማቆሚያዎች እና ተርሚናሎችን በዛሬው ዕለት ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ተደርገዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚህ ወቅት ÷ አዲስ አበባ እንደ ስሟ እያበበች ለነዋሪዎቿ ምቹ፤ ለጐብኚዎችም ሳቢ እየሆነች ነው ብለዋል፡፡
ዛሬ ከአራዳ ጀምሮ፣ በሜክሲኮ፣ ለገሀር፣ ሳር ቤትና የአፍሪካ ህብረት አካባቢ የከተማዋን ገጽታ ይበልጥ የሚያሻሽሉ ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን ተናግረዋል፡፡
ግንባታዎቹ ለወጣቶችና ሴቶች የሥራ ዕድል የሚፈጥሩ፣ የትራፊክ ፍሰቱን የሚያሳልጡ፣ የሚያዘምኑና የአካባቢዎቹን ውበት የሚጨምሩ እንደሆኑ አስረድተዋል፡፡
በዚህ መሰረትም በባሻ ወልዴ ችሎት አካባቢ ፓርኪንግን እንዲሁም አፍሪካ ህብረት ጋር ዘመናዊ የገበያ ማዕከል ፣ ፓርኪንግና የሕጻናት መዝናኛ ለአገልግሎት ክፍት ተደርጓል ብለዋል።
የአፍሪካ ህብረት የገበያ ማዕከል እና ፓርኪንግ በ28 ሺህ 500 ሜትር ስኩዌር መሬት ላይ የተገነባ ዘመናዊ ማዕከል ነው፡፡
ማዕከሉ ሁለት ቤዝመንትና ፕላዛ፣ 250 ሱቆች እና 250 መኪኖችን በአንድ ጊዜ ማስተናገድ የሚችል ሲሆን÷ የሕጻናት መጫወቻ፣ 45 መጋዘን፣ የመጸዳጃ ክፍሎች፣ ፋውንቴይን፣ አምፊ ቴአትርና ፕላዛ በውስጡ ይዟል፡፡
በባሻ ወልዴ ችሎት ላይ የተሰራው ሌላኛው ዘመናዊ የመኪና ማቆሚያና ገበያ ማዕከል ካፍቴሪያዎች፣ ሱፐርማርኬት፣ ሱቆች፣ ሬስቶራንቶች፣ ፕላዛ እና የመኪና ማቆሚያ አለው፡፡
ሁለቱ ማዕከላት ዘመናዊ የእሳት አደጋ መቆጣጠሪያና፣ የደህንነት ካሜራ የተገጠመላቸው፣ ለሕጻናት፣ ለአቅመ ደካሞችና አረማያን ምቹ እና አካታች መሰረተ ልማት እንዳላቸው ተመላክቷል፡፡
በጥቅሉ ከሜክሲኮ እስከ ለገሃር እና አፍሪካ ህብረት ዙሪያ ባሉ አካባቢዎች እስከ 3 ሺህ 769 ተሽከርካሪዎችን ማስተናገድ የሚችሉ የፓርኪንግና ተርሚናል መሰረተ ልማቶች እንደሚገኙ የከተማዋ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ለፋና ዲጂታል ገልጿል።
ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!