አዲስ አበባ፣ መስከረም 11፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ያሳየነውን የመቻልና የመፈፀም አቅም በሌሎች የልማት ዘርፎችም እንደግማለን አሉ የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ።
የሕዳሴ ግድብ መጠናቀቅን ተከትሎ በአፋር ክልል በተለያዩ ወረዳዎች ሲደረግ የነበረው ሕዝባዊ የድጋፍ ሰልፍና የደስታ መግለጫ ዛሬ በሠመራ ከተማ ተካሂዷል።
አቶ አወል አርባ በሰልፉ ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት እንዳሉት÷ በሕዳሴ ግድብ ያሳየነውን የመቻልና የመፈፀም ትብብራዊ ተግባራችንን በተለያዩ የልማት ዘርፎችም እናስቀጥላለን።
የሕዳሴ ግድብ ኢትዮጵያ የጀመረችውን መጨረስ እንደምትችልና አሸናፊ መሆኗን ያስመሰከረችበት፤ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን አሻራ ያረፈበት ዳግማዊ ዓድዋ መሆኑን ገልጸዋል።
የሕዳሴ ግድብ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካውያን የብርሃን ተስፋን ያሳየ፣ የቀጣናው መተሳሰር የተጠናከረበት የወል ትርክታችን ህያው ምስክር መሆኑንም ተናግረዋል።
የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አብዱ ሙሳ በበኩላቸው÷ ግድቡ እኛ ኢትዮጵያውያን በይቻላል መንፈስ ጠንክረን ከሰራን ሁሉንም ጉዳዮች ማሳካት እንደሚቻለን ያሳየንበት ነው ብለዋል።
በሠመራ ስታዲየም በተካሄደው የድጋፍ ሰልፍ ላይ ልዩ ልዩ ትርዒቶችና ባህላዊ ጭፈራዎች የቀረቡ ሲሆን÷ የሕዳሴን ግድብና የትብብር ስኬትን የሚያሳዩ መልዕክቶችም በመፈክር መልክ መቅረባቸውን የዘገበው ኢዜአ ነው።
በድጋፍ ሰልፉ ላይ የክልሉ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!