አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 4፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ላይ የተፈጠረው ንጋት ሰው ሰራሽ ሐይቅ ለኢትዮጵያ ሰፊ በረከት ይዞ መጥቷል አሉ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ሃብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር)።
የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስቴር የንጋት ሐይቅ ረቂቅ ማስተር ፕላን ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቢሾፍቱ ከተማ የውይይት መድረክ እያካሄደ ይገኛል።
ሃብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) በመድረኩ እንዳሉት÷ አሁን ያለው ትውልድ እና አመራር የዓባይ ወንዝ የኢትዮጵያ ኩራት እንዲሆን አድርጓል።
ኢትዮጵያዊያን በጋራ ቆመን ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፈውን ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እውን አድርገናል ያሉት ሚኒስትሩ÷ ለታሪክ የሚተላለፍ ዐሻራ ለማኖር በትብብር መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
ግድቡ የኤሌክትሪክ ኃይል ከማመንጨት በላይ መሆኑን ገልጸው÷ ከኢትዮጵያ ባለፈ ለጎረቤት ሀገራትም በረከት ይዞ የመጣ መሆኑን ተናግረዋል።
በግድቡ ላይ የተፈጠረው በአፍሪካ 4ኛው ግዙፉ የንጋት ሐይቅ ለሀገራዊ ኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል።
ይህንን ለማሳካትም የንጋት ሐይቅ ማስተር ፕላን ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል።
ከ70 በላይ ደሴቶች ያሉትና ከ74 ቢሊየን ሜትሪክ ኪዩብ በላይ ውሃ የያዘው ንጋት ሐይቅ ለኢትዮጵያ ሰፊ በረከት መያዙንም ተናግረዋል።
ሐይቁ ለዓሳ ሀብት ልማት፣ ትራንስፖርት እና ቱሪዝምን ጨምሮ ለዜጎች ሰፊ የስራ ዕድል የመፍጠር አቅም ያለው መሆኑን አንስተው÷ ባለድርሻ አካላት በማስተር ፕላን ዝግጅቱ ላይ አስፈላጊውን ግብዓት እንዲሰጡ ጠይቀዋል።
በአቢይ ጌታሁን
ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!