የሀገር ውስጥ ዜና

እንደ ባሌ ያለ ሁሉን ነገር በአንድ የያዘ ድንቅ ምድር አይቼ አላውቅም – ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)

By Yonas Getnet

October 20, 2025

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 10፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በሕይወት ዘመኔ እንደ ባሌ ያለ ሁሉን ነገር በአንድ የያዘ ድንቅ የተፈጥሮ ምድር አይቼ አላውቅም አሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሶፍ ኡመር ወግ በሚል ርዕስ ከቀድሞ እና በሥራ ላይ ካሉ አመራሮች ጋር ተወያይተዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚህ ወቅት ÷ ላለፉት ሶስት ቀናት በባሌ ምድር በርካታ አስደናቂ እና አስደማሚ የተፈጥሮ ጸጋዎች መመልከታቸውን አንስተዋል፡፡

በቆይታቸውም ለምን ደሃ ሆንን የሚለው ጥያቄ እንዳሳሰባቸው እና የተመለከቱት ኃብት እና ተፈጥሮ ከእኛ አልፎ ለሌላ የሚተርፍ እንደሆነ መገንዘባቸውን ተናግረዋል፡፡

ትውልዱ ነቅቶ ከንትርክ በመውጣት በሀገሩ በመስራትና በማልማት ከልመና የሚወጣበትን መንገድ ማበጀት ላይ መነጋገር እንደሚያስፈልግ አንስተዋል።

ኢትዮጵያውያን ነቅተን ሀገራችን ላይ ሰርተን ሌላን መርዳት ሲገባን እኛ ያለንበት ሁኔታ እና የተሰጠን ነገር አብሮ አይሄድም ሲሉም አስረድተዋል፡፡

በበርካታ ሃገራት ተዘዋውሬ ተመልክቻለሁ፤ ነገር ግን እስካሁን በሕይወት ዘመኔ እንደ ባሌ ያለ ሁሉ ነገር በአንድ የያዘ ምድር አይቼ አላውቅም ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፡፡

ይሄ ተሰጥቶን መሰረታዊ ነገሮችን ማሟላት ያልቻልነው ለምንድን ነው? ለሚለው ጥያቄ መልስ አላገኘሁለትም ሲሉም በአጽንኦት ጠይቀዋል፡፡

በእነዚህ ጉዳዮች መወያየትና እኛ ያበላሸነውን፤ ያላስተካከልነውን ጉዳይ አርቆ አልሞ በማሰብ ለነገይቱ ኢትዮጵያ ተስፋ እንዲሆን ለማስተካከል መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡

ኢትዮጵያውያን እና ትውልዱ ተምሮ በመሰባሰብ ካለንበት ሁኔታ ወጥተን እና ሀገር ሰርተን በጋራ ለመኖር መወያየት አስፈላጊ መሆኑን አስጽንዖት ሰጥተዋል።

ውይይቱ በሶፍ ኡመር ዋሻ እንዲካሄድ የተፈለገው ታሪካዊ በመሆኑ እና እግረ መንገዱን ትውልድ እንዲመለከተው ለማድረግ በማለም ነው ብለዋል፡፡

በዮናስ ጌትነት

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!