አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 12፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በጋምቤላ ክልል ጋምቤላ ከተማ የተገነባው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆነ።
በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ወ/ሮ አለሚቱ ኡሞድ እና የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ኮሚሽነር መኩሪያ ኃይሌን (ዶ/ር) ጨምሮ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
መኩሪያ ኃይሌ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት፤ ለዜጎች የሚሰጡ መሠረታዊ አገልግሎቶችን የማዘመን ስራ በትኩረት እየተከናወነ ነው።
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የተቀላጠፈ አሰራርን በመከተል የተገልጋዮችን እርካታ የሚፈጥር መሆኑን ገልጸው፤ በተቋማት የሚታየውን የአገልግሎት አሰጣጥ ችግር ለመፍታት መፍትሄ መሆኑን ተናግረዋል።
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀልጣፋ አገልግሎቶችን ለማቅረብ፣ የአገልግሎት ፈላጊዎችን ጊዜ እና ወጪ ለመቆጠብ እንዲሁም የተገልጋዮችን እርካታ ለማሳደግ ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል።
ወ/ሮ አለሚቱ ኡሞድ በበኩላቸው፤ ለዲጂታል ኢትዮጵያ ጉዞ አጋዥ የሆነው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የተቋማትን አገልግሎት በአንድ ቦታ ለመስጠት ያስችላል ነው ያሉት።
ተገልጋዩ ለእንግልትና ወጪ እንዳይጋለጥ የሚያስችል መሆኑን ገልጸው፤ አገልግሎቱ በስድስት የክልል ተቋማትና በሁለት የፌደራል ተቋማት በ29 አገልግሎቶች ስራ መጀመሩን ተናግረዋል።
የክልሉ ፐብሊክ ሰርቪስና ሰዉ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ላክደር ላክባክ፤ ማዕከሉ የአገልግሎት አሰጣጥ ባህልን የሚያሳድግ መሆኑን ማነገራቸውን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ለፋና ዲጂታል አረጋግጧል።
ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡- YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook FBC (Fana Broadcasting Corporate S.C.) Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook WMCC TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!