ቢዝነስ

ኢትዮጵያ የዓለም የንግድ ድርጅትን ለመቀላቀል አስፈላጊ መስፈርቶችን ለማሟላት ቁርጠኛ ናት – ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር)

By Adimasu Aragawu

October 22, 2025

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 12፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ኢትዮጵያ የዓለም የንግድ ድርጅትን ለመቀላቀል አስፈላጊ መስፈርቶችን ለማሟላት ቁርጠኛ ናት አሉ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር)።

ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) በዓለም የንግድ ድርጅት እና በባለብዙ ወገን ጉዳዮች የአሜሪካ ረዳት የንግድ ተወካይ ኒል ቤክ ጋር የኢትዮጵያን የዓለም የንግድ ድርጅት አባልነት ድርድርን በተመለከተ ተወያይተዋል።

በውይይታቸውም ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያን የዓለም የንግድ ድርጅት አባልነት አስመልክቶ የተካሄደውን የስድስተኛ የስራ ቡድን ስብሰባ ውጤት እና ከስብሰባው በኋላ የተከናወኑ ቁልፍ ማሻሻያዎችን አብራርተዋል።

ኢትዮጵያ የአባልነት ድርድሩን በካሜሩን ያውንዴ በፈረንጆቹ መጋቢት 2026 በሚካሄደው የዓለም የንግድ ድርጅት 14ኛ የሚኒስትሮች ጉባዔ ወቅት ለማጠናቀቅ ያላትን ቁርጠኝነት ገልጸዋል።

የአባልነት ሂደቱ በተቀመጠ የጊዜ ገደብ ለማሳካት በሚል ብቻ የሚመራ እንዳልሆነ ጠቅሰው፤ በተጨባጭ ስራ፣ በትጋት እና የንግድን መዋቅራዊ ለውጥ የማምጣት አቅምን በሚገነዘብ አመራር ነው ብለዋል።

ኢትዮጵያ ድርጅቱን ለመቀላቀል አስፈላጊ የሆኑ መስፈርቶችን ለማሟላት ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል።

የገበያ አቅርቦት ላይ እየተደረጉ ያሉ የሁለትዮሽ ድርድሮች የሚገኙበትን ደረጃ እና ኢትዮጵያ ከአባል ሀገራትና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች የምታገኘውን ከፍተኛ ድጋፍ በመጥቀስ፤ አሜሪካ በዚህ ረገድ የተጠናከረ ተሳትፎ እንድታደርግ ጠይቀዋል።

ለኢትዮጵያ መጠነ ሰፊ ሪፎርም እውቅና የሰጡት ኒል ቤክ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የዓለም የንግድ ድርጅት አባል ለመሆን የሄደችበትን ርቀት አድንቀዋል።

ኢትዮጵያ የጀመረችውን ጉዞ አጠናክራ እንድትቀጥል በማበረታታት አሜሪካ ተገቢውን ተሳትፎ እንደምታደርግ ገልጸዋል።

የዓለም የንግድ ድርጅት አባል ለመሆን ማሟላት ያለባትን መስፈርት በግልፀኝነት ለማሳወቅም ቃል ገብተዋል።

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!