አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 17፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባዔ የተለያዩ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ተጠናቅቋል፡፡
ከጥቅምት 11 ጀምሮ ሲካሄድ የቆየው ምልዓተ ጉባኤ ስለቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና የምጣኔ ሀብት ዕድገት፣ ስለሀገር ሰላምና አንድነት፣ ስለቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ሰፊ ውይይት አድርጓል፡፡
የሲኖዶሱ ምልዓተ ጉባዔ መጠናቀቁን አስመልክቶ መግለጫውን የሰጡት የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ÷ በትግራይ የሚገኘው ሕዝበ ክርስቲያን ሕዝባችንና ወገናችን ስለሆነ አብያተ ክርስቲያናቱና ገዳማቱም የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ ሀብቶች ናቸው ብለዋል።
አሕጉረ ስብከቱም የተደራጁት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በመሆኑ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሕግና ቀኖና ተጠብቆ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ልዕልና ተከብሮ፣ የመዋቅር ግንኙነቱን ወደ ቀደመ ቦታው እንዲመለስ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሰላም፣ የአንድነትና የይቅርታ በር ክፍት መሆኑን ከመግለጽ ጋር ቅዱስ ሲኖዶስ በክልሉ ለሚገኙት አባቶች፣ ካህናትና የሰላም ጥሪውን ማስተላለፉን አብራርተዋል።
ነባሩና ጥንታዊው የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ገድል እንደተጠበቀ ሆኖ “ገድለ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ” በሚል ያለአግባብ በአንድ ግለሰብ ተዘጋጅቶ እየተሠራጨ ያለው መጽሐፍ በሊቃውንት ጉባኤ ተመርምሮ ያለበት ግድፈትና የስሕተት ትምህርት በሙሉ የቤተ ክርስቲያኗን አስተምህሮ የማይወክል ሆኖ በመገኘቱ በቅዱስ ሲኖዶሱ ተወግዟልም ነው ያሉት።
የቤተ ክርስቲያኗ የአንድነት መዋቅር የበለጠ ተጠናክሮ ለትውልድ እንዲሻገር፣ ሕዝቡም ደኅንነቱና ሰላሙ ተጠብቆ እንዲኖር ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ጀምሮ ሁሉም የቤተ ክርስቲያን መምህራን፣ ካህናት፣ መነኮሳትና መነኮሳይያት የበኩላቸውን እንዲወጡ በማሳሰብ ጉባኤው ዓመታዊ ስብሰባውን ማጠናቀቁንም አመላክተዋል፡፡
በነፃነት ፀጋይ
ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!