አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 23፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የኢትዮጵያ እና አውሮፓ ህብረት ኢንቨስትመንት ፎረም ከነገ ጥቅምት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በፈረንሳይ ፓሪስ ከተማ ይካሄዳል፡፡
የገንዘብ ሚኒስቴር ለፋና ዲጂታል እንደገለጸው ÷ ፎረሙ የኢትዮጵያ እና አውሮፓ ህብረትን ዘርፈ ብዙ ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር ያስችላል፡፡
መድረኩ በአቪዬሽን፣ በታዳሽ ሃይል፣ በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ መሰረተልማት እና በዲጂታል ቴሌኮሙኒኬሽን ኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ ያተኮረ መሆኑ ተመላክቷል፡፡
ከዚህ ባለፈም የኢትዮጵያን ፈጣን የኢኮኖሚ እድገትና እያደረገች ያለውን ሪፎርም በማስረዳት የንግድ ትብብርን ለማጠናከርና ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ጉልህ ሚና እንዳለው ተጠቅሷል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዮስ (ዶ/ር) ÷ ፎረሙ ኢትዮጵያና የአውሮፓ ሀገራት በመሰረተ ልማት፣ በፈጠራ እና አካታች የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ ለሚሰሩት ሥራ ወሳኝ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል፡፡
የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ በበኩላቸው ÷ ኢትዮጵያ አዲስ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን ትግበራ ላይ መሆኗን አስረድተዋል፡፡
ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርምን እና የ10 ዓመቱ የልማት እቅድን በመተግበር የማይናወጥና ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ እየገነባች መሆኑንም አመልክተዋል፡፡
የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት የግል ዘርፉ ይህንን የልማት እቅድ ለማሳካት ዋና የልማት አጋር መሆኑን ነው ያብራሩት፡፡
የሜዴፍ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፊሊፕ ጉቶር ÷ የአውሮፓ የንግድና ኢንቨስትመንት ተቋማት ኢትዮጵያ ትልቅ አቅም እንዳላት ይገነዘባሉ ብለዋል።
ኢትዮጵያ ከአፍሪካ በፍጥነት በማደግ ላይ ያለ ኢኮኖሚ ያላት ሀገር ብቻ ሳትሆን በአረንጓዴ ልማት፣ ዲጂታል እና ትራንስፖርት መሰረተ ልማት ለመገንባት ባላት አቅም ተመራጭ መሆኗን ጠቁመዋል።
ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!