ቢዝነስ

በክልሉ ገበያን ለማረጋጋት የተጀመሩ የቅዳሜና እሁድ ገበያ ቦታዎችን ለማስፋፋት እየተሰራ ነው

By Adimasu Aragawu

November 12, 2025

አዲስ አበባ፣ ሕዳር 3፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በክልሉ ገበያን ለማረጋጋት የተጀመሩ የቅዳሜና እሁድ ገበያ ቦታዎችን ለማስፋፋት እየተሰራ ነው አለ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ፡፡

የቢሮው ኃላፊ አቶ ታሪኩ አካሉ ለፋና ዲጂታል እንዳሉት÷ የኑሮ ውድነትን በቁጥጥር ብቻ በዘላቂነት ችግሩን መፍታት አይቻልም።

ስለሆነም አማራጭ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን በማስፋፋት የኑሮ ውድነት ጫናን ለመቀነስ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።

በዚህም በክልሉ 8 ነባር፣ 5 አዲስ እና 19 የምሽት ገበያ ቦታዎች በአጠቃላይ 32 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን የማጠናከር ተግባራት በ2018 የመጀመሪያ ሩብ ዓመት መከናወናቸውን አመላክተዋል።

የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ሕብረተሰቡ በአካባቢያቸው ተመጣጣኝ በሆነ ዋጋ እንዲያገኙ በማድረግ የኑሮ ጫናን በማቃለል ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እያበረከቱ መሆኑንም ጠቁመዋል።

በገበያዎቹ የግብርና ምርቶችን ጨምሮ የተለያዩ ሸቀጦች በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረቡ እንደሚገኙም አቶ ታሪኩ ተናግረዋል።

የህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድ እንቅስቃሴ የኑሮ ውድነት እንዲባባስ የሚያደርግና ክልሉ ከሚያመርታቸው ምርቶች ተገቢውን የኢኮኖሚ ጥቅም እንዳያገኝ የሚያደርግ በመሆኑ የቁጥጥርና ክትትል ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን አስረድተዋል።

በአድማሱ አራጋው

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!