አዲስ አበባ፣ ሕዳር 7፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የዩክሬን ፕሬዚዳንት ቮሎዲሚር ዘለንስኪ የመንግስት ኢነርጂ ኩባንያዎች በአዲስ መልኩ እንደሚዋቀሩ አስታውቀዋል።
ፕሬዚዳንቱ ይህንን ውሳኔ ይፋ ያደረጉት የኢነርጂ ኩባንያዎች የስራ ኃላፊዎች በሙስና በመዘፈቃቸው የተነሳ የኢነርጂ ዘርፉ ችግር ውስጥ መውደቁ ከተገለጸ በኋላ ነው።
ሀገሪቱ ከሩሲያ ጋር በገባችበት ጦርነት የተነሳ የኢነርጂ ዘርፉ ፈተና ውስጥ በወደቀበት በአሁኑ ሰዓት የኢነርጂ ኩባንያዎቹ 100 ሚሊየን ዶላር ያህል ገንዘብ ማባከናቸው በምርመራ ተደርሶበታል።
ይህ የኩባንያዎቹ የሙስና ቅሌት በዩክሬናውያን ዘንድ ቁጣ መፍጠሩ ተመላክቷል።
ፕሬዚዳንት ዘለንስኪ ጉዳዩን አስመልክቶ በኤክስ ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ በኩባንያዎቹ ላይ ከሚደረገው ሁለገብ የፋይናንስ እንቅስቃሴ ኦዲት ጎን ለጎን የማኔጅመንት ለውጥ ይደረጋል ብለዋል።
የኩባንያዎቹ የሙስና ቅሌት ዋና ማዕከል የሆነው መንግስታዊው የኒውክሌር ኩባንያ ‘ኢነርጎአቶም’ በሳምንት ጊዜ ውስጥ አዲስ አማካሪ ቦርድ እንደሚሰየምለት ተናግረዋል።
ጉዳዩን እየተከታተሉ ያሉ የመንግስት አካላት ከህግ እና ጸረ ሙስና ተቋማት ጋር ተቀናጅተው በመስራት የኢነርጂ ዘርፉን ቀውስ ውስጥ የከተተቱ ሰዎች በሙሉ ተጠያቂ ለማድረግ መሰራት እንዳለበት ፕሬዚዳንቱ ትዕዛዝ መስጠታቸውን ቢቢሲ ዘግቧል።
ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!