አዲስ አበባ፣ ሕዳር 8፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የዋና ጽ/ቤት ኤርጎኖሚክስ ሥራ የተቋም ግንባታ ራዕይና ሥነ ምግባር ሲገናኙ መፍጠር የሚቻለውን እመርታ ያሳየ ነው አሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ጽ/ቤቱን ቀድሞ ከነበረበት በመለወጥ ወደ ኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ቀድሞ ሕንጻ ያዘዋወረበትን ሁኔታ ጎብኝተዋል።
በዚህ ወቅትም ኢንስቲትዩቱ ያደረገው ጽ/ቤቱን የማደስ ሥራ ለኢትዮጵያ በከፍተኛ ደረጃ ዓይን ገላጭና አዲስ ዕይታን የሚያሳይ ለሥራ ምቹ የሆነ ወጣቶች ረጅም ሰዓት ሊሰሩ የሚችሉበት ተቋምና ስፍራ ሆኗል ብለዋል።
አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲቲዩት በወቅቱ በተቋም መልክ ሲመሰረት ብዙዎች የገዙት ሐሳብ እንዳልነበረ፤ ይሁን እንጂ የሰው ልጅ የሚያስብበትን መንገድና ይቻላል የሚለውን ሐሳብ የሚያይበትን መንገድ እየቀረጸ መምጣቱን ተናግረዋል።
ከዚህ ቀደም አዲስ ዕውቀት፣ አዲስ ልምምድና አዲስ ፈጠራ ሲፈጠር ያንን ለማወቅና ለመከተል የነበረው ጉጉት፣ ዝግጁነትና ዕሳቤ አናሳ ስለነበረ ጥሩ ተከታይ መሆን አልቻልንም ነው ያሉት፡፡
አሁን ላይ ግን ሁኔታዎች መቀየራቸውን አንስተው÷ የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ በአፍሪካ ደረጃ ሊወዳደር የሚያስችል አሰራር የሚከተል ተቋም መሆኑን ተናግረዋል።
በዚህም ተቋሙ በርካታ ምርቶችን በማምረት በተለይም በጤና ዘርፍ የጡት ካንሰር ልየታ ላይ ትልቅ ውጤት ማምጣቱንና ይህም በዘርፉ አዋቂዎች ዘንድ ተቀባይነት ያገኘና በዓለም አቀፍ ጆርናል የወጣ ዕውቅናን ያገኘ ምርት መሆኑን ገልጸዋል።
በግብርና ዘርፍ ደግሞ የቡናና ሌሎች አዝርዕቶች በሽታን መለየት የሚያስችል መሳሪያ ማምረት መቻሉን ጠቁመው÷ ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችሉ በርካታ የልየታ አቅሞች በምርት ደረጃ መገንባታቸውን አብራርተዋል።
በሕዝቡ ቅሬታ የሚነሳበትን በአገልግሎት ዘርፍ ከ100 በላይ አገልግሎቶች የሚሰጠውን የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ሥርዓት የሰራው አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ እንደሆነ ጠቅሰዋል።
በዚህም ሥርዓቱን በራስ አቅም በመገንባት ብዙ ሚሊየን ዶላርን ማትረፍ መቻሉን ገልጸው÷ የጉምሩክ ሥርዓቶችን የማዘመን ሥራን ጨምሮ ብዙ ተቋማት ላይ እየተሳተፈ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
ተቋሙ “አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ለሁሉም” በሚል መሪ ሃሳብ ለሁሉም ሰዎች መገልገል፣ ማገዝና መጥቀም እንዲችል በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑን አመላክተዋል።
በአድማሱ አራጋው
ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!