የሀገር ውስጥ ዜና

በክልሉ ጠንካራ የፖሊስ ተቋምና አመራር ለመገንባት የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል አለበት – አቶ አረጋ ከበደ

By Adimasu Aragawu

November 17, 2025

አዲስ አበባ፣ ሕዳር 8፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በአማራ ክልል ጠንካራ የፖሊስ ተቋምና አመራር ለመገንባት የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል አለበት አሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ።

የክልሉ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ “ከጂኦ ስትራቴጂክ ኩስመና ወደ ታደሰ ቁመና” በሚል መሪ ሐሳብ ለከፍተኛና መካከለኛ የፖሊስ አመራሮች የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ አካሂዷል።

አቶ አረጋ ከበደ በመድረኩ እንደገለጹት÷ ጂኦ ስትራቴጂ የሚያስገኘውን ጥቅምና ተግዳሮት ላይ ለሁሉም ሕብረተሰብ ሰፊ ግንዛቤ ለመፍጠር እየተሰራ ነው።

ኢትዮጵያ ከቀይ ባህር በቅርበት የምትገኝና የድንበር ተሻጋሪ ወንዞች ባለቤት በመሆኗ ከዓለም ማህበረሰብ በእጅጉ የተሳሰረ የጂኦስትራቴጂ እድልና ተግዳሮት ያላት መሆኑን ተናግረዋል።

በዚህም ሀገራችን ያወጣችውን የጂኦስትራቴጂ ፖሊሲና እቅድ በአግባቡ በመምራት ያለንን እድል ወደ ድል በመቀየር ብሔራዊ ጥቅሞቻችንን ማስጠበቅ የሁላችንም ኃላፊነት ነው ብለዋል።

ፖሊስ ወንጀልን በመከላከልና የክልሉን ሰላም በማፅናት ለብሔራዊ ጥቅም መጠበቅ ኃላፊነቱን ሊወጣ ይገባልም ነው ያሉት።

በክልሉ ጠንካራ የፖሊስ ተቋምና አመራር ለመገንባት ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልፀው÷ ይህም ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አመልክተዋል።

የክልሉ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ ዋና አዛዥ ኮሚሽነር ጄኔራል ዘላለም መንግስቴ (ዶ/ር) በበኩላቸው÷ የሚሰጠው ስልጠና የፖሊስ አመራሩን ለላቀ ተልዕኮ ለማዘጋጀት የሚያስችል ነው ብለዋል።

በዚህም የክልሉን ወቅታዊና ነባራዊ ሁኔታ በመገንዘብና ሰላምን ለማጠናከር የበኩላችንን ድርሻ ለመወጣት የሚያስችል መሆኑን ተገንዝቦ ስልጠናውን በአግባቡ መከታተል ይገባል ማለታቸውን የዘገበው ኢዜአ ነው።

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!