አዲስ አበባ፣ ሕዳር 10፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ከ700 በላይ የቅድመ ማጣሪያ ተፎካካሪዎች መካከል የተለዩ 16 ከዋክብትን ይዞ የጀመረው የፋና ላምሮት ምዕራፍ 21 ውድድር በመጪው ቅዳሜ ቀጥሎ ይካሄዳል።
የምዕራፉ አራተኛ ሳምንት ውድድር ላይ የምድብ ሁለት ሰባት ተወዳዳሪዎች ከዛየን ባንድ ጋር ስራዎቻቸውን በሁለት ዙር ያቀርባሉ።
ለ13 ሳምንታት በሚዘልቀው በዚህ ምዕራፍ ተወዳዳሪዎች በተለያዩ ሳምንታት በራሳቸው፣ በዳኞች እና በተመልካቾች የሙዚቃ ምርጫ ብርቱ ፉክክር ያደርጋሉ።
የሙዚቃ ባለሙያዎች እና ተመልካቾች ባልተገደበ አጭር የጽሑፍ መልዕክት በሚሰጡት ድምጽ ተወዳዳሪዎቹ የሚዳኙ ይሆናል።
በምዕራፉ ለፍፃሜ ለሚደርሱ አራት ተወዳዳሪዎች የ1 ሚሊየን ብር ሽልማት የተዘጋጀ ሲሆን፤ ለፋና ላምሮት 6ኛው የአሸናፊዎች አሸናፊ ውድድርም በቀጥታ ያልፋሉ።
የምዕራፍ 21 ውድድር በመጪው ቅዳሜ ከ6:00 ጀምሮ በቀጥታ ስርጭት በፋና ቴሌቪዥን፣ በፋና+፣ በፋና ፌስቡክ፣ በፋና ዩቲዩብ እና ቴሌግራም ገጾች እንዲሁም በ www.fanamc.com ይከታተሉ።
በ8222 አጭር የጽሑፍ መልዕክት የተወዳዳሪዎችን ኮድ በመላክ እየተዝናኑ ድምጽ በመስጠት የዳኝነቱ አካል ይሁኑ።
ፋና ላምሮት ከ2011 ዓ.ም መጨረሻ ጀምሮ የበርካታ ባለተሰጥኦ ድምፃውያን መፍለቂያ በመሆን ለኪነ ጥበብ ዕድገት አሻራውን እያኖረ ይገኛል።
በለምለም ዮሐንስ