የሀገር ውስጥ ዜና

በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከ370 ሺህ በላይ ተማሪዎች የቅድመ መደበኛ ትምህርት እየተከታተሉ ነው – ትምህርት ቢሮ

By Adimasu Aragawu

January 08, 2026

አዲስ አበባ፣ ታሕሣሥ 30፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከ370 ሺህ በላይ ተማሪዎች የቅድመ መደበኛ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ ነው አለ የክልሉ ትምህርት ቢሮ።

የቢሮው ምክትል ኃላፊ ማቲዮስ ማልደዮ ለፋና ዲጂታል እንዳሉት÷ የቅድመ መደበኛ ትምህርት ለአጠቃላይ መማር ማስተማር ሂደት መሰረት ከመሆኑ አንጻር ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራበት ይገኛል።

በዚህም የቅድመ መደበኛ ትምህርት በመንግሥት መጀመሪያ ደረጃ፣ በግል እና ለብቻቸው በተቋቋሙ የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶች እየተሰጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

በክልሉ ከ2 ሺህ በላይ የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶች እንደሚገኙ ገልጸው÷ ከእነዚህ ውስጥ 1 ሺህ 700 በላይ የመንግሥት እና ከ300 በላይ የግል መሆናቸውን ጠቁመው÷ ከ370 ሺህ በላይ ተማሪዎች ትምህርታቸውን እየተከታተሉ ናቸው ብለዋል።

የቅድመ መደበኛ ትምህርት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ልዩ ትኩረት እንደተሰጠው በመግለጽ÷ በክልሉ ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ ኢኒሼቲቭ ተቀርጾ ሰፊ እንቅስቃሴ እየተደረገ ይገኛልም ነው ያሉት።

በዘርፉ ከሚስተዋሉ የመማሪያ ክፍሎች እጥረትና ከደረጃ በታች የመሆን ችግሮችን ለመቅረፍ በየዓመቱ ከ300 በላይ ደረጃቸውን የጠበቁ ትምህርት ቤቶች በመገንባት በ5 ዓመታት ከ1 ሺህ 500 በላይ ትምህርት ቤቶችን ለአገልግሎት ለማብቃት እየተሰራ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል።

በዘርፉ የሰለጠኑ መምህራንን ቁጥር ለማሳደግ በመደበኛ፣ በአጫጭር ስልጠና እና በሳምንቱ የመጨረሻ ቀናትና በክረምት መርሐ ግብር ስልጠናዎች እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል።

ተማሪዎች በምግብ እጥረት ምክንያት ከትምህርታቸው እንዳይስተጓጎሉም በክልሉ ከ150 በላይ ትምህርት ቤቶች የምገባ መርሐ ግብር እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው÷ በቀጣይም መርሐ ግብሩን ለማስፋፋት መታቀዱን ጠቁመዋል።

በዮናስ ጌትነት

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡- YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation Facebook FBC (Fana Broadcasting Corporate S.C.) Facebook https://web.facebook.com/fanasport Facebook WMCC Telegram t.me/fanatelevision Website www.fanamc.com TikTok www.tiktok.com/@fana_television WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29 Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment Amharic Podcast YouTube www.youtube.com/@fanamcpodcast በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!