የሀገር ውስጥ ዜና

አርሶ አደሮቻችን እያመረቱ ብቻ አይደለም፤ ከመዋጮዎቻቸውም እሴት እያፈሩ ይገኛሉ – ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)

By Melaku Gedif

February 19, 2026

አዲስ አበባ፣ የካቲት 12፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) አርሶ አደሮቻችን እያመረቱ ብቻ አይደለም፤ ከመዋጮዎቻቸውም እሴት እያፈሩ ይገኛሉ አሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ ÷ የጊቤ ዲዴሳ የገበሬዎች የኅብረት ሥራ ማኅበርን የሥራ እንቅስቃሴ መጎብኘታቸውን ገልጸዋል፡፡

በ1996 ዓ.ም የተመሠረተው የጊቤ ዲዴሳ የገበሬዎች የኅብረት ሥራ ማኅበር 207 የመጀመሪያ ደረጃ ማኅበራትን ያቀፈ ነው ብለዋል።

167 ሺህ ገበሬዎችን የሚያገለግለው ማኅበሩ አሁን ላይ የግብርና ግብዓቶችን ከማቅረብ ተሻግሮ የምርት እሴትን ወደመጨመር ማደረጉን አስረድተዋል፡፡

ማኅበሩ በቅርቡ ዘመናዊ የእህል ወፍጮ ያቋቋመ ሲሆን ÷ በዚህም በቀን 1 ሺህ 200 ኩንታል የበቆሎ ዱቄት የማምረት አቅም እንዳለው አመልክተዋል፡፡

በ2 ነጥብ 8 ሄክታር መሬት ላይ የተገነባው ፋብሪካ ለአካባቢው ጊዜያዊ እና ቋሚ የሥራ እድሎች መፍጠሩንም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) ጠቅሰዋል፡፡